ከዛሬ አርባ አራት ዓመት በፊትና በዃላ በኢትዮጵያ ውስጥ የራሳቸው መታወቂያ ያላቸው ሶስት አይነት መንግሥታት ተመስርተው ለማየት በቅቻለሁ።ከዛሬ አርባ አራት ዓመት በፊት የነበረው ዘውዳዊ ስርዓት፣በነገሥታት የሚመራ ስርዓት የነበረ ሲሆን የፖለቲካና የኤኮኖሚው መሰረቱ አገር በቀል የሆነ፣ከባእዳን ቁጥጥር ነጻ የሆነ በባላታዊ ስርዓትላይ መሰረት የጣለ ነበር።ኢትዮጵያም አገር ወዳድ አመለካከት ባላቸው መሪዎች ፍላጎት የምትመራ አገር ነበረች።ይህ ስርዓት ከባዕዳን ጋር የነበረው ግንኙነት የወዳጅነት ሳይሆን የእምቢ ባይነትና ባለማጎብደድ ብሎም ለቅኝ ገዢ ወራሪ ሃይል ያልተንበረከከ በመሆኑ ጠላቱ የበዛና ብቻውን የቀረ ነበር።ኢትዮጵያ ቁጥራቸው በበዛ ጠላቶች ተከባ እንድትፈራርስ ደባና ሴራ የሚመታባት አገር ነበረች።የአውሮፓውያን የመስፋፋትና የቅኝ አገዛዝ ወረራም በተደጋጋሚ ተሰንዝሮባት መሪዎቹ በሕዝባቸው ሃይልና በአላቸው የጦር መሣሪያ፣ጋሻና ጦር ብቻ በየአቅጣጫው የመጣውን ጠላት ተፋልመው ነጻነታቸውን ሳያስደፍሩ እንደ ሃገር በነጻነት ለመኖር በቅተዋል።በዚህ የትንቅንቅ ሂደት አንድ አገር ሊደርስበት የሚችለው የእድገት ደረጃ ሳይታይ መቅረቱ የሚያስገርም አይሆንም።
እድገትና ስልጣኔ ሰላምና አንድነትን ይጠይቃል።ያ በሌለበት አገር ስልጣኔ አይታሰብም።ምንም እንኳን የኤኮኖሚ እድገትና መሻሻል ባይኖርም ሕዝቡ በባዕዳን ክርን እንዳይደቆስ፣ክብርና ዜግነቱን እንዳያጣ የሚንከባከብና የሚያስከብር ስርዓት ነበር።ነገስታቱ ከወራሪ ባእዳን ጋር የሚያደርጉት ትንቅንቅ እንዳለ ሆኖ በውስጥም የስልጣን ሽኩቻ ላይ በመሰማራታቸው የረጋ ስርዓትና ቀጣይነት ያለው እድገት ለማምጣት አልቻሉም።ዘመነ መሳፍንት ያደረሰውን ቀውስና ስብራት ለመጠገን የብዙ ጊዜ ሰላም ይጠይቅ ነበር።አጼ ቴዎድሮስ በመሳፍንቱ የተናጋውን አንድነት በሃይል አስከበሩ፣ከውጭ ወራሪዎችም ጋር በተለይም ከእንግሊዞች በኩል የሚቃጣውን የወረራ ጉዞ በዲፕሎማሲና በጉልበት ተጠቅመው እስከሕይወተ ፍጻሜያቸው ድረስ ተከላከሉ። አጼ ዩሃንስ በቱርክና በግብጽ .በእንግሊዞች የተቀመረ ወረራ ጋር ተጋፍጠው ህይወታቸውን አሳልፈው ሰጡ፣አጼ ምኒሊክም ከውጭ ወራሪዎች ጋር የገጠማቸው ችግር ቀላል አልነበረም፤ ድንበር ጥሶ የመጣውን የጣሊያን ጦር በመቋቋምና ድል በመምታት አቅማቸውና ሁኔታው እስከፈቀደላቸው ድረስ ወደመጣበት በመመለስ ለመጀመሪያ ጊዜ የአውሮፓ ወራሪ ሃይል በጥቁር ሕዝብና መሬት ላይ ተዋርዶ እንዲመለስና ለሌላው ጭቁን ሕዝብ የትግልና የነጻነት አርአያ እንዲሆን አድርገዋል።አልፎ አልፎ ጸጥታና ሰላም ሲሰፍን ባላቸው እውቀትና አቅም አገራቸውን ለማሳደግና የሕዝቡን ኑሮ ለማሻሻል ቦዝነው አያውቁም።ለአንድ አገር መሻሻልና እድገት የተማረ ሕዝብና እውቀት ዋና መሰረቱ ስለሆነ በዚያ መስክ ትምህርት እንዲስፋፋ የመጀመሪያውን መሰረት ጥለዋል። አገራቸው ከሰለጠነው ዓለም ጋር እንድትጓዝ ዘመናዊ አሰራሮችንና የእድገት በሮችን የከፈቱት እሳቸው ነበሩ።የስልክ መስመር፣የፖስታ አገልግሎት፣የመብራት ሃይል፣የመጓጛዣ መኪና፤ሆቴል፣ የፎቶግረራፍ ሙያ፣የባቡር መስመር፣ የባንክ አገልግሎት፣ ሆስፒታል፣የመንግስት አሰራር በካቢኔ ሚኒስትሮች መልክ እንዲደራጅ ያደረጉት እሳቸው ናቸው።አገራቸው በጎሳ ተከፋፍላ ከምትጓዝ በአንድ አጠቃላይ ማእከላዊ መንግስት ስር እንድትተዳደር የአጼ ቴዎድሮስን ፈለግ ተከትለው በተግባር የተረጎሙ መሪ ናቸው።ይህ አካሄድ ከሌላው አገር ማእከላዊ መንግስት አመሰራረት የተለዬ አይደለም።ስልጣን እናጣለን ከሚሉት የከባቢ መልከኞችና ባላባቶች ጋር ጦር ያማዘዘ ሂደት ነበር።
እንደ አባ ጅፋር አይነቶቹ ኦሮሞውን ወገናቸውን እየለጎሙ በባርነት ከሚሸጡ ባለባቶች ጋር ያደረጉት ትግል ቀላል አልነበረም።አንዳንዶቹን በማሳመንና በማባበል ሌሎቹን ደግሞ በሃይል አንድነትን ከሚቀበሉ የጎሳ መሪዎችና ተወላጆች ጋር በመተባበር ኢትዮጵያ ዳግም እንድትነሳ አድርገዋል።ይህ የውህደትና የአንድነት እርምጃ በአንዳንዶቹ ግምት የተደረገ ወረራ ነው በማለት እስከዛሬ ድረስ ቅርሾ በመያዝ አሁን ላለንበት ወቅት ለውጩም ጠላት በር የከፈተ እንቅፋት ሆኗል።በአጼ ቴዎድሮስም ሆነ በአጼ ምኒሊክ እንዲሁም ከሳቸው በዃላ በነበሩት መሪዎች የተካሄደው አገርን የመገንባትና ድንበር የማስከበር እርምጃ እሳቸውን ተክተው ስልጣኑን የተረከቡት ንግስት ዘውዲቱና ልጅ እያሱም ቢሆኑ ምንም እንኳን በውስጥ ቀውስ ተጠምደው ለአገራቸው የረባ ነገር ሳይሰሩ በአጼ ሃይለስላሴ አድማ ተመተው ከስልጣን እስከተወገዱበት ድረስ ፈለጉን ተከትለው ተጉዘዋል።ስልጣን ከተፈሪ መኮንን (ሃይለሥላሴ) እጅ ከገባ በዃላም የተጀመረውን ለማስቀጠል አገሪቱ ሰላም አላገኘችም።በአጼ ምንሊክ ተዋርዶ የተመለሰው የጣሊያንና የነጮቹ ጎራ የበቀል እርምጃ ለመውሰድ ለዳግመኛ ጊዜ ወረራ አካሄደ።ከአምስት ዓመት ትግል በዃላ በዓለም የተፈጠረው ሁኔታ አግዟቸው የነጮቹ ጎራ እርስ በርሱ በጥቅም ሲጋጭ የወራሪው የጣሊያን መንግሥት ከጀርመኑ የሂትለር መንግሥት ጋር አብሮ በመቆሙ የሌሎቹ ጠላት ሆኖ በወገኖቹ ነጮች በእንግሊዞች እርዳታ ከኢትዮጵያ ተሸንፎ ለመውጣት በቃ።ንጉስ ሃይለስላሴ ከሚኒልክ ተረክበው ሊቀጥሉ የፈለጉትን የእድገት ጎዳና የውጭ ሃይሎች ለመቀልበስና ፍላጎታቸውን ለማሟላት በጦር ሜዳ ሊሳካላቸው ባለመቻሉ በስውር መንገድ እየገቡ ሙከራ ማድረጋቸውን አላቆሙም።በመሳፍንቱና በነገሥታቱ መካከል የሚነሳውን አለመግባባትና የሥልጣን ሽኩቻ እያራገቡ፣አንዱን በማወደስና በመርዳት ሌላውን በመውቀስ የተንኮል ሴራ ሲያውጠነጥኑ ኖረዋል።ያም ቢሆን ለሚፈልጉት ግብ አላደረሳቸውም። ሆኖም ግን በእርስ በርሱ ግጭት የብዙ ሰው ህይወትና የአገር ንብረት ወድሟል። አለመተማመንና ቅርሾም በመፍጠሩ ሁሉም በሙሉ ልቡ ወደአገሩ ከማተኮር ይልቅ ወደ ሚደግፈውና የከባቢ ስሜት እየገባ የራሱን አገር ነጻነት ከማስከበር ይልቅ በውጭ ሃይሎች እየተረዳ የሥልጣኑ ባለቤት ለመሆን በሚያስችለው የባንዳ ተልእኮ ውስጥ ተሰማርቶ ብዙ ጉዳት እንዳደረሰ በታሪክ ታይቷል።ይህ አድራጎት ጎልቶ የታየው በጣሊያን ወረራ ወቅት ነበር።በዚህ የጣሊያን ወረራ ከጎኑ ተሰልፈው ያገራቸውን ሰንደቅ አላማ ቀደው በጣሊያኖቹ ባንዲራ የተኩና ተሸክመው በወገኖቻቸው ላይ ግፍ የፈጸሙ ዜጎች ብዙ ናቸው።ከነሱም መሃል አሁን በስልጣን ላይ የሚገኙት አባቶችና አያቶች ይጠቀሳሉ።ከጦር ሜዳ አንስቶ በሰላይነት የተሰማሩ እንደነበሩም ታሪካቸው ይመሰክራል።ጣሊያን የነሱን እርዳታ ባያገኝ ኖሮ አዲስ አበባ ድረስ ሰተት ብሎ ለመግባትና አገሪቱን ከሞላ ጎደል ለመቆጣጠር ባልቻለም ነበር። በቆራጥ መሪዎቹና በአገር ወዳዱ ሕዝብ መስዋእትነት የጣልያንና የባንዳዎቹ ፍላጎት ግን በአጭሩ ተቀጭቶ ኢትዮጵያም መልሳ በራሷ አገር ወዳድ መሪዎች ልትመራ ቻለች።ከዚህ የጦርነት ስብራት በዃላ አገሪቱ ለመንሰራራት ትልቅ ፈተና ገጥሟት ነበር።ጣልያንና እንግሊዝ የረጩት የልዩነት መርዝ በአንዳንዱ የአገሪቱ ዜጋ አስተሳሰብ ላይ ጎጆውን ሰርቶ አልፏል።የአንድነት ፍላጎቱን ለማመንመንና ከኢትዮጵያዊነት ይልቅ የባዕዳነትን ስሜት እንዲያስተናግድ የሚያስችለው አስተሳሰብ በአንዳንዶቹ ላይ ተጽእኖ በማድረጉ አገሪቱ በህብረት ልትገነባ የሚያስችላት ሃይል እንዳይኖራት አድርጓል።
ለአሁኑም ልዩነትና የጎጥ ፖለቲካ ስርዓት ምክንያት ሆኗል።ከውጭ ወራሪ ሃይል ጋር ከሚደረገው ትንቅንቅ በተጨማሪ በአገር ውስጥ ግጭቶች እንዲነሱ ተደርጎ የአገር ሃብትና የሰው ሃይል ባላስፈላጊ የእርስ በርስ ግጭት እንዲመናመንና ጭራሽ ወደባሰ ድህነት እንዲያመራ ምክንያት ሆኗል።ከጣሊያን ቀጥሎ በሶማሊያ ወራሪ ሃይል ጋር ተደጋጋሚ ጦርነት ተደርጓል፣በራያና አዘቦ፣በጎጃም፣በባሌ የተደረጉት የእርስ በርስ ውጊያዎችም የአገሪቱን ሃብት በማድቀቁና የልዩነት መንፈስ በማዳበሩ በኩል የየራሳቸውን አስተዋጽኦ አድርገዋል። አንድ ጊዜ ሲበርድ ሌላ ጊዜ ሲያገረሽበት በሚሄደው የውስጥ ችግር የተወጠረው መንግሥት እፎይ ብሎ ሙሉ ለሙሉ ለልማት እንዳያተኩር እንቅፋት ሆኖበት ነበር። ከዚያም በላይ የነበረው ስርዓት ባህልና እምነቱ በቀድሞ አስተሳሰብ የተተበተበ በመሆኑ እርቆ ሊሄድ አልቻለም።ዘመናዊ አስተሳሰብና ትምህርት ለማስፋፋት የሚፈልጉት ንጉስም ከቤተክህነትና ከባላባቶች አካባቢ ብዙ ፈተናና ተቃውሞ ነበረባቸው።
የሕዝቡ ኑሮ ከፍልስፍናና ከፈጠራ ይልቅ በተፈጥሮና በመለኮታዊ ችሮታ ላይ የተመካ ነበር።ዝናብ ሲጠፋ ይራባል፣ወንዝ እያለው በመስኖ የመጠቀም ችሎታ አላዳበረም።
እርግጥ ነው የነበረው ስርዓት ሙሉ ለሙሉ የሕዝቡን ፍላጎት የሚያሟላ ነበር ማለት አይቻልም።አገር ከመውደዱና የአገርን ነጻነት ከማስከበሩ ጎን ለጎን አገሪቱን በሚያሻሽለው የዴሞክራሲ ጥያቄና ሰለሕዝቡ መደረግ የሚገባቸውን በተለይም የባላባቱንና የጭሰኛውን ግንኙነት ለመቀየር የመሬትን ባለቤትነት የሚያረጋግጠውን የዜጋ መብት ያከበረ አልነበረም።ዃላ ቀር ከነበረው የባላባት ስርዓትና የምርት ግንኙነት የሚያላቅቅ የተሻለ የኤኮኖሚ መዋቅር የሚያመቻች አገር ወለድ ተቋማትና አሠራር አላዳበረም።በመሆኑም እያደር ድህነት እንጂ መሻሻል አልታየበትም ነበር።ይህም አንዱና ዋናው የተቃውሞ መቀስቀሻ ሆነ።ተቃውሞው ሕዝቡን በሙሉ ያሳተፈ ሳይሆን በተማረውና በነቃው ዙሪያ የሚካሄድ ነበር፤ለተቀሰቀሰው ተቃውሞ ግን ጥይት አልተኮሰም፣ሰላማዊ ሰልፈኞችን በአደባባይ አልረሸነም።ግፋ ቢል አስሮና በወላጆች ምክር ከመልቀቅ ያለፈ ቅጣት አልቀጣም። የአጼ ሃይለስላሴ መንግሥት እንደዛሬዎቹ የውጭ እርዳታና ብድር አያገኝም ነበር።ለመጀመሪያ ጊዜ የመቶ አስር ሚሊዮን ዶላር ከፍተኛ የውጭ አገር እርዳታና ብድር የተገኘው ንጉሱ ቻይናን በጎበኙበት ጊዜ ከቻይና ነበር።በተረፈ በስዊድን መንግሥት እርዳታ በደቡብ በእርሻ ስራ የልማት ዘርፎችና ፣ከደቾች ሱካር ፋብሪካ፣ከተንዳሆ የእንግሊዞች የጥጥ እርሻ ተጨማሪ የጎላ ድርሻ የነበራቸው የውጭ አገር ተቋማት አልነበሩም።አሜሪካ በወታደራዊ መስክ ጀርመን በፖሊስ ሰራዊት ተቋም ከሚሰጡት ድጋፍና ስልጠና ሌላ በኤኮኖሚው ዘርፍ ጎልቶ የታዬ ተሳትፎ አልነበራቸውም።የአሜሪካኖቹም እርዳታ ቢሆን ከጂኦፖለቲክ ጥቅማቸው አንጻር ነበር።
ወደ መጨረሻው ላይ በአገሩ ተወላጆች የተጀመሩ ሰፋፊ የእርሻ ስራዎች ነበሩ።እነሱም ያተኮሩት በአገር ውስጥ ገበያ በሚሆኑ ምርቶች ላይ ሳይሆን በውጭ አገር ገበያ ለሚቀርቡ ምርቶች በሰሊጥ፣ቦለቄና በመሳሰሉት ላይ በመሆኑ ከዓለም የዋጋ ግሽበት ጋር አብረው ከሰሙ፤ የተረፉትም ደርግ ስልጣኑን ሲይዝ ነጠቃቸው።
የውጭ ወራሪና ታሪካዊ ጠላቶች የተከሰተውን ችግርና ሕዝብ አለመርካት በመጠቀም የነበረውን አገር ወዳድ ስርዓት እንዲወገድ ሌት ተቀን ይሰሩ ነበር። ከነዚህም ውስጥ ወጣቱን በሃይማኖትና በፖለቲካ መስመር ውስጥ ማሰለፍና መቀስቀስ ቀላሉና ማራኪው መንገድ ነበር።ወጣት ትውልድ አዲስ አስተሳሰብና ለዕድገት ያለው ፍላጎት ከፍተኛ በመሆኑ ለለውጥ የተዘጋጀ የህብረተሰብ ክፍል ነው።ያንን ፍላጎቱን በሚጥም መልክ እየቀሰቀሱ ማሰለፍ ቀላሉ ዘዴ ነበር።በመጀመሪያ ወጣቱ በምእራባውያን አስተሳሰብ እንዲቀረጽ በልዩ ልዩ ዘዴ ዘመቻ ተደርጎበታል።በሙዚቃ፣በፊልም፣በአለባበስ፣..ወዘተ በዘመናዊነት ስም ከኢትዮጵያዊነት ባህልና አስተሳሰብ እንዲርቅ ተደርጓል።የስርዓቱም ተወካዮች አንዳንዶቹ በጎና መልካሙን መለየት፣ከወቅቱም ጋር መሄድ ተስኗቸው በያዙት ዃላ ቀር መንገድ ስለቀጠሉበት ለልዩነቱና ለደረሰው ስብራት የበኩላቸውን አበርክተዋል።ለብዙ ጊዜ ውስጥ ለውስጥ እየተብላላ የቆየው ብሶትና የለውጥ ፍላጎት በውስጡ ኢትዮጵያን የመጥላትና ኢትዮጵያዊ ያለመሆንን ስሜት ለሚያራምዱት አገር በቀል ጠላቶች ቦታና እድሉን ፈጠረላቸው።
በዓለም ላይ የተከሰተው የፖለቲካ ቀውስና በተለይም በኢትዮጵያ የተከሰተው ድርቅ የአገሪቱን ሁኔታ አባብሶት የዘውዳዊ ስርዓት መዋቅሩን ለማናጋት ቻለ።ለዘመናት ሰፍኖ የኖረው አገር ወዳዱ የባላባታዊ ስርዓት ፈተና ውስጥ ገባ፤ፈተናውን ማለፍ አቅቶት ወደቀ።በለውጥ ሽፋን የወታደር አምባገነን ቡድን ቦታውን ቀማው።
ይህ የወታደር ቡድን አነሳሱ ላይ ቀናና አገር ወዳድ ነበር፣ሥልጣንም ይዞ ለመቆየት ዓላማ አልነበረውም።በዃላ ላይ ለስልጣን በሚፎካከሩ ሁለት ቡድኖች በኢሕአፓና በመኢሶን መካከል በሚደረገው ትንቅንቅ ውስጥ ገባና አንዱ አንዱን በመሆን እርስ በርሱ ተናክሶ የመኢሶንን ቡድን በመደገፍ የሚራመደው የነመንግሥቱ ሃ/ማርያም ቡድን በአሸናፊነት ስልጣኑን ጠቅሎ ያዘ።የተማሪው ትግል የወለዳቸው እነዚህ ሁለት ድርጅቶች በመጀመሪያው ላይ አንድ የነበሩ ሲሆን የሚያራምዱትም አንድ አይነት የሶሺያሊስት ዝንባሌ ያለው ፍልስፍና ነበር።ለአንዳንድ ጥያቄዎች በሚሰጠው መልስ ላይ ልዩነት ተፈጥሮ ልዩነቱን ተወያይቶ ከማሶገድ ይልቅ የጠላትነት ጎራ ተፈጠረና አንዱ ሌላውን ለማጥፋት ቆርጦ ተነሳ።ለዲሞክራሲ ለውጥ ይታገሉ የነበሩት እራሳቸው ችግርን በዲሞክራሲ መንገድ መፍታት ተሳናቸው።የአንደኛው ክንፍ አባላት ጸረ ዲሞክራሲ የሆነውን የወታደር አምባገነን ተራማጅ አድርገው በመቀበል አብረው ለመስራት ወሰኑ።ሌላው ከዳር ሆኖ የወታደሩን ቡድን ከውስጡ ለማፈራረስ ሌላ ዘዴ ቀመረ።የሁለቱ ቡድኖች ቀውስ በደርግ ውስጥ ሰርጎ ገባና አገር አቀፍ ቀውስ ሆነ።ደርግም በአነሳሱ ላይ ይዞት የነበረው አገር ወዳድ መልኩ ተለወጠና እየደበዘዘ የስልጣን ወዳድነት ባህሪ በተጫነው ጥቂት ቡድን በኩል ስልጣኑ መንግስቱ ሃ/ማርያም ለሚባለው ለፍላፊ፣ ጨካኝና በዝቅተኛነት ስሜት በቀልና ጥላቻ ላደረበት አምባገነን የግል ንብረት ሆነ።በውስጡና ከውጭ ለሚነሱት ጥያቄዎች ሁሉ መልሱ ጥይት ሆነ።ይኸው አምባገነን አካሄዱ ያላማራቸው ጸባዩን የሚያውቁት የሐርር ሶስተኛ ክ/ጦር አባላት ቤተሰቡን መያዣ አድርገው ለጥያቄ ሲፈልጉት፣ብትፈልጉ ቀቅላችሁ ብሏቸው እንጂ አልመጣም ብሎ የመለሰ፣የራሱን ስልጣን ከወለዳቸው ልጆቹ አብልጦ የሚያይና የሚመርጥ አረመኔ መሆኑን ከጧቱ ያሳዬ ነበር።ግን ይህ አባባሉ ከቤተሰቡ ይበልጥ አገሩን እንደሚወድ ተደርጎ ተመነዘረለትና አገር እስኪያጠፋና እስኪጠፋ ድረስ መብትና ስልጣን ተሰጠው።እርግጥ ነው በሱ አይፈረድበትም! መንግስቱ ሃ/ማርያም በጦሩ የነበረው ቦታ የመሳሪያ ግምጃ ቤት አላፊ ሆኖ ጥይት መቁጠርና መሳሪያ መጠገን ስለሆነ ከቃታና ከሰደፍ የበለጠ በቅርብ የሚያውቀው ችሎታና እውቀት አልነበረውም።ለፍቅርም ለጠብም የሚመዘው ያንኑ አብሮት ውሎ የሚያመሸውን ጠመንጃ ነበር።ከማን ጋር ነሽና ተሆኛለሽ ጤና ነው።ይህ ፈላጭ ቆራጭ እውቀተ ቢስ ሰው አጋጣሚ ሆኖ ባገኘው ዕድል በሕዝቡና በአገሪቱ ላይ የፈጸመው ወንጀል ሌሎቹ የቀድሞ መሪዎች የፈጸሙት ቢደመር የሱን እሩብ አይሆንም።ለአገር ይሞታሉ እንጂ አገር ገለው አላለፉም።ወጣቱን ጨፍጭፎ ለገደለበት ጥይት ዋጋ ያስከፈለ አረመኔ መንግሥት በኢትዮጵያ መሬት ላይ ሲበቅል ደርግ የመጀመሪያው ነው።ለመገንጠል ጫካ ገብተው ይታገሉ የነበሩትን “የብሔር ነጻ አውጭዎችን”ቀስፈው የያዙትን፣ለአገራችው ክብርና አንድነት ለማስከበር የተሰለፉትን የጦር መኮንኖችና ወታደሮች ጥያቄ አቀረባችሁ በማለት በጦር ሜዳ እየገደለ ሰራዊቱን መሪ አልባ አድርጎ ያስጠቃና በመጨረሻውም ከነጮች ጋር ተደራድሮ አገሪቱን አሁን ላለው አውሬ ቡድን አሳልፎ ሰጥቶ አገር ጥሎ የኮበለለ ፣ በኢትዮጵያ ሕዝብ ስነልቦና ላይ የፍርሃትና የሽብር ድባብ ያሰፈነ፣ኢትዮጵያን በታሪኳ ያላየችውን የመሪ ሽሽት ያስተዋወቀ አሳፋሪ ከንቱ ሰው ነው። ይህንን ከንቱና አሳፋሪ እንደ ጀግና ቆጥረው የሚያሞካሹት፣የፈጸመውን የአገር ክህደትና ወንጀል የሚኮሩበት የሱ ቢጤዎችና የስርዓቱ ተጠሪዎች በየአገሩ ተበትነው ሲመጻደቁ ይሰማል።የእሱ የሥራ ውጤት አገሪቱን አሁን በሥልጣን ላይ ላለው ለተገንጣዮች ቡድን አስረክቦ መሄድ ሲሆን የአገሪቱ አንድነት በባሰ አደገኛ ደረጃ ላይ እንዲደርስ ከፍተኛ ድርሻ አበርክቷል።
ይህ አሁን በስልጣን ላይ ያለው ቡድን ከሃምሳ ዓመት ወዲህ በአገራችን ውስጥ ከሰፈኑት መንግሥታዊ ስርዓቶች የተለዬ፣አገር ወዳድነት ስሜት የሌለው፣ገና ከጅምሩ በውጭ ሃይሎች የተቀሰቀሰና የተረዳ፣የጣሊያንንና የሌሎቹን የኢትዮጵያ ጠላቶች ፍላጎት በተዘናጋ መልኩ ለማስፈጸም የተፈጠረ ስብስብ ነው።ይህ ስብስብ እንደጣሊያንና እንግሊዝ አገሪቱን በጎሳና በክልል ከፋፍሎ ጠንካራና አንድ አገር እንዳትሆን ሌትተቀን የሚሰራ ቡድን ነው።ለጎሳ መብትና እኩልነት ቆሜለሁ እያለ ጎሳ ከጎሳ እንዲባላና እንዲጋጭ እያደረገ ጠንካራ ብሔራዊ ስሜት እንዳይኖር የሚያደርግ የውጭ ተልእኮውን በሚገባ የሚፈጽም የባንዳ ስብስብ ነው። ኢትዮጵያ የምትባል አገር ፈርሳ ኤርትራ፣ትግሬ፣ኦሮሞ፣አማራ፣ሶማሌ፣ጋምቤላ፣አፋር፣…ወዘተ የሚሉ የመንደር መንግሥታት ተመስርተው እርስ በእርሳቸው ሲዋጉ እንዲኖሩ ቀምሮ የተነሳ ቡድን የሚቆጣጠረው መንግሥት ነው። ይህንንም በተግባር አሳይቷል፤ኤርትራን አስገንጥሎ በማግስቱ ወደ ጦርነት የሄደ ቡድን ነው።ከሌሎቹም ጋር ግብግብ ከገጠመ ውሎ አድሯል።አገር ከማፈራረሱም ጋር አገር የመበዝበዝንም ተግባር በማከናወኑ ከሌሎቹ ስርዓቶች የተለየ አድርጎታል።የመሪ ሌባ የሰፈነበት ስርዓት በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ እንደዚህ ታይቶና ተሰምቶ አይታወቅም። ይገላል፣ይዘርፋል፣አገሪቱን ለውጭ አገር ጥቅምና ቁጥጥር አሳልፎ የሰጠ፣ድንበር እየቆረሰ የሚያስረክብ፣እንደመሪ ሳይሆን እንደሰውና ዜጋ ሊታይ የማይገባው የአውሬ ስብስብ ነው።
የውጭ ባላደራ መንግሥት በመሆኑ ከሌሎቹ የተለየ እውቅናና ድጋፍ አለው።ከላይ እንደተገለጸው ኢትዮጵያ እንደ አንድ ነጻ አገር እንዳትኖር ለተደረገባት የወረራ ሙከራ አጻፋውን ሰጥታ አሳፍራ የመለሰች፣ለሌሎች አገራት የትግልና የነጻነት ምሳሌ ሆና የኖረች በመሆኗ ወራሪዎች ጥርሳቸውን የነከሱባት አገር ነበረች፤ያንን በቀል በአገር በቀሉ ከሃዲ ቡድን ሊካሱ ችለዋል።ለዚህ ባለውለታ ቡድን እንኳንስ የፖለቲካ ድጋፍና የገንዘብ እርዳታ ቀርቶ ሌላም ቢያደርጉ አይከብዳቸውም።በኢትዮጵያ ላይ ብቻ ሳይሆን በሌሎች አገሮች ለሚያካሂዱት ዘረፋና ወረራ አስከባሪ ቀድሞ ደራሽ በሩ መሆኑም ውለታ እየሰራላቸው ነው።በዚህም የባንዳ ተግባሩ የሚሻውን ድጋፍ እየሰጡ በስልጣኑ ላይ እንዲቆይ ይመርጣሉ።አገር ወዳድ ሃይል በኢትዮጵያ ምድር ላይ እንዲወለድ አይሹም።ይህ የሚረዱት መንግስት ቢወድቅ፣ሰላምና ጸጥታን ለማስከበር በሚል ስም ወታደሩ ሥልጣኑን እንዲወስድ ወይም የውጭ ሃይል እንዲገባ ከማድረግ አይመለሱም፡፤ይህ ካልሆነ ኢትዮጵያ ተበታትና በተለያዩ የክልከል የጎሳ መሪዎች መዳፍ ስር ወድቃ ቁጥጥራቸውን ለማስቀጠል በሚረዳ መልኩ ቢሆን ይመርጣሉ።ለዚህ ኢራቅ ምሳሌ ናት።የኩርዲስታንና የሌላው አካባቢ መነጣጠል ያንን ያረጋግጣል።
ለሰብአዊ መብት ቆመናል እያሉ የሰው ልጅ በአደባባይ ሲረሸን፣እናት በልጇ አስከሬን ላይ ተቀምጣ እንድትዘፍን ስትገደድ፣ወጣቱ በሥራ አጥነት ተስፋ ቆርጦ ሲሰደድ እያዩና እየተጠየቁም ጆሮ ዳባ ልበስ ከማለትም አልፈው ለዚሁ ወንጀለኛ መንግሥት ተብየው ቡድን የማበረታቻ የገንዘብ እርዳታና የፖለቲካ ድጋፋቸውን መስጠቱን መርጠዋል።እዚህ ላይ ነው ማን ለምንና ለማን ጥቅም መቆሙ የሚታየው።
አሁን በስልጣን ላይ ያለው ቡድን በስልጣን ላይ ለመቆየት ካልቻለ አገሪቱን በታትኖ ለመጥፋት እቅድ እንዳለው ከከፍተኛ ባለስልጣናቱ ውስጥ ሁለቱ ፣አባይ ጸሃዬና ስዩም መስፍን የተባሉት ወንጀለኞች በቅርቡ በሰጡት ቃለምልልስ አረጋግጠዋል።ለዚህ አመቺ የሚሆነው ደግሞ ሕዝቡ ተለያይቶ በክልልና በጎሳ ትግል ውስጥ ከተሰለፈ ነው።በዚህ ጉዞ ደግሞ ማንም አትራፊ ሳይሆን የሚጎዳበት ነው፤በአንዱ ኪሳራ ላይ ሌላው ሊጠቀምና በሰላም ሊኖር አይችልም።አገራችን የእብድ ቤት ትሆናለች ማለት ነው።ያ ሁኔታ ደግሞ የውጭ ሃይሎች ሰርገው እንዲገቡና የሚፈልጉትን እንዲያደርጉ ዕድልና በር ይከፍታል።አደጋውን ለመቀልበስ አገር ወዳዱና ለውጥ ፈላጊው ኢትዮጵያዊ ያለው ምርጫ አንድና አንድ ብቻ ነው።በጎሳ መለያየቱን ትቶ በአንድ አገር ዜግነት መቆምና ያለውን ስርዓት ማሶገድ። የውጭ አገር ጠላቶች ለሚፈልጉት የመገነጣጠል ዓላማ ሳይመች፣የተለያየ መሆኑን በሚያበስር መልኩ የተለያየ ባንዲራ ስር መሰለፉን ትቶ በአንድ ሰንደቅ ዓላማ ስር መሰለፍ፤በውጭ አገር መንግሥታት ላይ ከመተማመን ይልቅ በራስ መተማመን።የዘመነ መሳፍንትን ጊዜ መንፈስ ከሚያንጸባርቀው የአካባቢና ጎሰኛ ፖለቲካ ወጥቶ አገር አቀፍ ፖለቲካ መንደፍና መከተል።ለተመሳሳይ የጎሳ ስብስብ ጥቅምና ስልጣን የሚካሄደውን ዝግጅትና የተናጠል ጉዞ መንቀፍና ማክሰም።የጠላትን ሃይል ለመስበር በሚችለው የትግል ስልት መሰለፍ። እስከአሁን የታየውን የመጠላለፍ ጎጂ ተግባር አሶግዶ ተመሳሳይ የሆነ ዓላማና አቋም ያላቸው በአንድ ጣራ ስር እንዲሰለፉ ማድረግ፤የተቀጣጠለውን ሕዝባዊ ትግል በመርዳት መልክ በማስያዝና በማያያዝ እንዲቀጥል፣ብሔራዊ መልክ እንዲይዝ ማድረግ።በመንግስት ላይ የተከሰተውን የፖለቲካና የኤኮኖሚ ቀውስ እንዲፋፋም ጠንክሮ መስራት።የመንግስት ባለስልጣናትና ቤተሰቦች የአገርና የውጭ ባለሃብቶች ንብረት በሆኑትና ስርዓቱን በሚረዱ ተቋማትና የንግድ ድርጅቶች ላይ እቀባ ማስፈን። የመንግስት የለያይተህ ግዛን መመሪያ እጅ ለእጅ ተያይዞ ማክሸፍ።እወክለዋለሁ ከሚለው ሕዝብና ክልል መነጠል።በክፍተት ስርዓተአልበኝነት እንዳይከሰት ሕዝቡ በየቦታው ከሰራዊቱና ከፖሊስ ሃይሉ ወደ ሕዝቡ ከሚቀላቀሉት ጋር ሆኖ ሕግ አሰከባሪ አካል እንዲፈጥር ማድረግ። እነዚህን ተግባራት በስራ ለመተርጎም የሚችል አካል ለመፍጠር በአገር ውስጥ ሁሉን አቀፍ ጉባኤ በአስቸኳይ ማካሄድ የወቅቱ ተግባር መሆን ይኖርበታል።ሁኔታው ከእጅ ሳይወጣ በፍጥነት መፍትሔ መፈለግ አስፈላጊ ነው።በዚህ ግርግር ከሕዝቡ በስተጀርባ ሥልጣን እይዛለሁ ብሎ ማሰብና ከውጭ ሃይሎች ጋር መደራደር ዋጋ አይኖረውም።ሥልጣን ለመጨበጥ ቢቻል እንኳን ሁኔታውን ያባብሰዋል እንጂ ዘላቂ መፍትሔ አያመጣም፣ሕዝቡም አይቀበልም፤የሚቋምጡ ካሉ ባይሞክሩት ጥሩ ነው።
በአገርቤትና በውጭ አገር የሚገኙት ተቃዋሚዎች ግንኙነት መፍጠር አለባቸው።አገራችን የጥፋት ማእበል ውስጥ እንዳትገባ አገር አድን ሃይል መፍጠር ይኖርባቸዋል፤የሚፈጠረው ይህ አካል ከሁሉም የተውጣጣ ሲሆን እንደሽግግር መንግስትም ሆኖ ሊያገለግል ይችላል።
እነዚህ በአለፉት የአርባ አምስትና ከዚያም በላይ በሆኑት የዕድሜ ዓመታት ያየናቸው መንግሥታት ሲሆኑ ሶስቱም የሕዝቡን ፍላጎትና ጥያቄ መመለስ የቻሉ አይደሉም።ሦስቱም ሕዝብ መርጦና ፈቅዶ የሥልጣኑ ባለቤት ያደረጋቸው ሳይሆኑ በጉልበትና በታሪክ አጋጣሚ ከሥልጣን ወንበር ላይ የተቀመጡ ናቸው።ሁለቱ መንግሥታት አወዳደቃቸውም ሳያምር የቀረ ሆኗል።አሁን በመውረግረግ ላይ ያለው ቡድን እንዳለፉት ሁለቱ በሕዝቡ ትግል የሚወገድበት ጊዜ እሩቅ አይሆንም።
በተደጋጋሚ እንደታየው ለነዚህ ሦስት ስርዓቶች ዕድል የሰጠው የሕዝቡ አለመንቃትና አለመደራጀት፣ብሎም በአንድነት ቆሞ ወግዱ ሳይላቸው በመቅረቱ ነው።አሁን ግን ያለንበት ዘመንና የንቃተ ህሊናችንም ለነዚህ አይነቶቹ ስርዓቶች የሚመች አይደለም።እርግጥ ነው ሕብረተሰባችን ሙሉ ለሙሉ የነቃና የተደራጀ ነው አይባልም፤ግን ካሳለፈው መከራ ብዙ ትምህርት ቀስሟል።ወደተሻለ አቅጣጫ ሊመራ የሚችል የተደራጀ ጠንካራ ሃይል ባይኖረውም የሚፈልገውን ያውቃል።
አሁንም ያለፉት አይነት ስርዓቶች አይነት ለመተካት ፍላጎት ያላቸው አይጠፉም።በዘርና ባለፈ ቅርሾ ሰበብ የዘር ፖለቲካ የሚያናፍሱ አገሪቱንና ሕዝቡን ለአደጋ ሊያጋልጡበት የሚችለው ዕድል ከፍተኛ ነው።እራሳቸውን ትልቅ በማድረግም ከውጭ መንግሥታት ጋር እየተደራደሩ እራሳቸውን ለአገልጋይነት አጭተው ሕዝባቸውን መስዋእት ለማድረግ የተሰለፉም እንዳሉ አይካድም።
ከዚህና ካለፈው አይነት ስርዓት የተሻለ ለማምጣት የሚፈልጉና አገራቸው እንዳገር አንድነቷ ተጠብቆና ተከብራ የሕዝቡም ኑሮ ተሻሽሎ ማየት የሚፈልጉት እውነተኛ አገር ወዳዶችና የለውጥ ሃይሎች ሳያቅማሙ አንድነት ፈጥረው ካለፉት የተለዬ ስርዓት እንዲመሰረት መጣር አለባቸው።አገራችን ዳግመኛ ከጎሰኛ፣ ከአምባገነንና የውጭ ሃይሎች አሽከር ከሆነ ቡድን እጅ እንዳትገባ መጠንቀቅ ተገቢ ነው።
የሚመሰረተው ስርዓት፣በሕግ የበላይነት የሚያምን፣የዴሞክራቲክ መብቶችን የሚያረጋግጥ፣የዜጎችን እኩልነትና ፍትህን የሚያከብር፣በሕዝብ ተመርጦ በተወሰነ ጊዜ የሚወጣና የሚወርድ መንግሥትና መሪ እንዲኖር በሚያስችል አሰራርና ሕግ የሚመራ፣የአገሪቱን አንድነትና የሕዝቡን ልዑላዊነት የሚያስከብርና የሚያረጋግጥ መሆን ይኖርበታል።
ይህንን የሚቀበሉ ሃይሎች፣የፖለቲካ ድርጅቶች፣የሲቪክ ተቋማት፣ግለሰቦች፣የጉዳዩ ተካፋይ የሆኑ ሁሉም ዜጎች ከጎሳና ከሃይማኖት ነጻ የሆነ የሽግግር መንግሥት ለመመስረት በጋራ መምከርና መዘጋጀት የወቅቱ ተግባር መሆኑን ሊያውቁትና ሊቀበሉት ይገባል።የሽግግር መንግሥቱንም መመሪያና የአጭር ጊዜ መርሃግብር በጋራ መንደፍ ይኖርባቸዋል፤ስለሆነም ሰርገኛ መጣ በርበሬ ቀንጥሱ እንዳይሆን ነገ ዛሬ ሳይሉ አብረው ለመምከር አስቸዃይ ስብሰባ ሊጠሩ ይገባል።እንደተለመደው የስብሰባ ውድድርና መጠላለፍ እንዳይኖር ብዙሃኑ ቁጥጥር ሊያደርግባቸው ይገባል።
በተጨማሪም ህወሃት /ኢሕአዴግ ተቃውሞውን የአሸባሪዎችና የጥፋት ሃይሎች ሥራ ለማስመሰል፣እንዲሁም መውደቂያውን አስቦ በተንኮልና እኔ ከሞትኩ ከሚል እኩይ አሳብ በመነሳት በአንዳንድ ተቋማትና በግለሰቦች ላይ አደጋ በመጣልና በእሳት በማጋየት ተግባር ላይ ስለሚውል ያንን በማጋለጥና በእልህ ሕዝቡ በተመሳሳይ ተግባር ላይ እንዳይሰማራ ማስጠንቀቅ ያስፈልጋል። ማንኛውም ተቋም ከድል በዃላ ለአገሪቱና ለሕዝቡ ጥቅም በሚሰጡበት መልኩ እንዲደራጁ ማድረጉ ስለማይቀር ከውድመት ማዳን ብልህነት ነው።የሚጎዳውንና የሚጠቅመውን አስቀድሞ ማጤኑ በሳልነት ነው።በዛች አገር መሬት ላይ ያለንብረት ምንጩና መሰረቱ የአገሪቱ ሃብትና የህዝቡ ላብ ስለሆነ መውደም አይኖርበትም።
በአርባ አምስት ዓመታት ውስጥ ያየዃቸው የኢትዮጵያ መንግሥታት ጭማቂ ባህሪያት
የአጼ ሃይለሥላሴ መንግሥት የደርግ መንግሥት የህወሃት/ኢሕአዴግ መንግሥት
ንጉሳዊ ፈላጭ ቆራጭ ፣ ወታደራዊ አምባገነን፣ የዘረኞች አምባገነን
በፈሪሃእግዚአብሔር የሚመራ፣ በሕገጠመንጃ የሚመራ፣ በሕገአራዊት የሚመራ
ሕዝብ የሚያከብረው ፣ ሕዝብ ጠልቶት የሚፈራው፣ ሕዝብ አንቅሮ የተፋው
ለአስከሬን ክብር ያለው፣ ገሎ የጥይት ዋጋ የሚያስከፍል፣ ልጅ ገድሎ እናትን የሚደበድብ
ተቃዋሚውን በዱላ እንጂ የጭካኔ ባህል ያዳበረ ጥያቄና ለተቃውሞ ቦታና ዕድል የማይሰጥ፣
በጥይት የማይደበድብ ተቃውሞ በጥይት የሚመልስ የሚገል፣የሚያስርና የሚያሳድድ
ለሥልጣኑ ሙት ለሥልጣኑ ሙት፣ትዕግስተቢስ፣ ለሥልጣኑ ሙት፣ዘራፊ፣አገሩን የሚሸጥ
ሕዝቡን ያስከበረ፣ካለቪዛ በአውሮፓ የስደትን በር የከፈተ፣ሕዝቡን ስደትን እንደሙያና ሥራ የቆጠረ
የመዘዋወር መብት ያረጋገጠ፣ ለውርደት የዳረገ በወታደሩና በድሆች ስም የሚነግድ
ሕዝቡ በአገሩ ውስጥ ከዳር እስከዳር ፍርሃትና ሽብር የሰፈነበት ፍርሃትና የመበታተን አደጋ የሰፈነበት
የመንቀሳቀስ፣የመኖርና የመስራት ከግማሽ ሚሊዮን በላይ ጥላቻና ልዩነት የሚያራግብ ወ ነጻነቱን ያረጋገጠ፣አንጻራዊ ሰላም ወታደር አሰልፎ ጥቂት በዘር እንጂ በዜግነት የማያምን
የሰፈነበት ተገንጣዮችን መቋቋም የአገሪቱን መከላከያ ሃይል በዘር
በስልሳ ሽህ ቋሚ ወታደር ያገሩን አቅቶት የኮበለለ፣ አዋቅሮ ለማዋጋትና አገር
ዳር ድንበር ያስከበረ በኢትዮጵያ መሪዎች አፍርሶ ለመጥፋት የተዘጋጀ
ለአፍሪካ አንድነት መሠረት የጣለ ታሪክ ውስጥ አሳፋሪ የሆነ ለባዕዳን ጥቅም የቆመ