ከተፈራ ድንበሩ
ውሻ፡ አንተ ዝንጀሮ ከዚህ አካባቢ ብትሔድ ይሻልሃል፤ ሂድ! ሂድ! ሂድ! ነው የምልህ! ቶሎ ከዚህ አካባቢ ባትጠፋ ቦጫጭቄ ቦጫጭቄ ነው አፈር የማደርግህ!
ዝንጀሮ፡ እስቲ ሞክር! ዋጋህን ታገኛለህ! እኔ ብቻዬን ያለሁ መሰለህ? የኔ ሠራዊት አንድ ጊዜ ቢዘምትብህ አንተን ብቻ ሳይሆን ዘመድ አዝማድህን ሁሉ ፈጅተን ነው ለአውሬ እራት የምናደርገው!
ዉሻ፡ ይኸውልሃ! ፉከራህ ሁሉ ወደፍርሃት ተለውጦ ሠራዊት ከምትላቸው ጀሌዎችህ ጋር ዛፍና ገዳላገደልን የሙጥኝ ያልከው ታዲያ ለምንድነው? እስኪ ውጡ እና ኑ! እኛና እናንተ ይለይልናል! እኛ ሁለት ሆነን እናንተ ሃያ ሆናችሁ አገር እስኪሸበር በሲቃ እያስጮህናችሁ እያሳደድን እስከገደል አፋፍ ድረስ አደረስናችሁ፤ በራሳችሁ የምትተማመኑ ከሆነ ውጡ እስኪ! ቦቅቧቆች! ቅዘናሞች! ቂጣችሁ እስኪላጥ በየገደሉ ያንፏቀቅናችሁ እኛ ጌቶቻችሁ ነን፤ እመኑ።
ዝንጀሮ፤ አዎን የፈራነው እኮ እናንተ ውሾች እያነፈነፋችሁ ሰዎችን በኛ ላይ ስለምትጠሩብን ነው፤ እንዲህ እንድትጮኹብን ያደረጉትና እናንተን ለዚህ ዕድል ያበቋችሁ ሰዎች ናቸው እንዲህ እንድትፎክሩብን ያደረጓችሁ፤ እናንተ የምትቦርቁበት ሜዳ፤ ውሀ እየተንጣለለበት የተለያዩ እህሎች፣ አታክልቶች፣ ፍራፍሬዎች የሚመረትባቸውና ስፍር ቁጥር የሌለው የቀንድ ከብት እና ሌሎች እንሰሳት የሚረቡበትን ሜዳ ትተን በተራራማና ገደላገደል ላይ የምንኖረው ቀደም ሲል ሰዎች አሳደውን እና መድረሻ አሳጥተውን ነው እናንተን ለዚህ ያበቋችሁ። ያን ሁሉ አገር ምድር ትተንላችሁ በየቋጥኞችና ገደላገደል አፋፍ ላይ መኖራችን አንሶባችሁ ለምን አሁንም ደግሞ ታሳድዱናላችሁ?
ዉሻ ፤ የሌባ አይነደረቅ መልሶ ልብ ያደርቅ ይላል ሰው! ደግሞ ለምን ታሳድዱናላችሁ ትላለህ እንዴ? በየማሳው ላይ የምትሸመጥጡትን ሰብል ዘርታችሁታል? ከናንተ ተርፎና ታጭዶ የተከመረን ክምር በየአውድማው እየዘረጠጣችሁ የምትበሉት ባለርስት ሆናችሁ ነው ወይንስ የሌብነት ሙያችሁን ለመሸፋፈን ነው?
ዝንጀሮ፡ ዘረፋ የምንገባው ቢቸግረን ነው፤ ያን ሁሉ ሜዳ እና ለም አገር ሁሉ ትተንላችሁ በየጫካው ስንኖር ፍራፍሬ እንኳ እየለቀምን እንዳንኖር ጌቶቻችሁ እንደዋርካ፣ ዝግባ፣ እንኮይ ዶቅማ፣ ያሉትን ዛፎች ሁሉ እየቆረጡ ቀጋ፣ እንጆሪ፣ አጋምና ኮሽም ሳይቀር ቁጥቋጦውን ሁሉ እየመነጠሩ ደኑን ስላጠፉት የምንበላው የምንቀምሰው አጥተን በችጋር ስናልቅ ታዲያ ዝም ብለን ነው የምንሞተው?
ውሻ፡ እናንተ እርስበርሳችሁ እንኳ የማትስማሙ ጠባይም የሌላችሁ አስቀያሚዎች፤ እንደኛ ጠባይ ቢኖራችህ ኖሮ በየገዳላገደሉ እየተንፉዋቀቃችሁ አትኖሩም ነበር፤ እኛ ግን ታማኞች ስለሆን ኮርተን ተንቀባረን እንኖራለን።
ዝንጀሮ፡ አዎን አስቀያሚዎች ነን፤ በአስቀያሚነታችን አናፍርበትም፤ እናንተ ለጌቶቻችሁ ባሪያ በመሆን ከነሱ የተራረፈውን ፍርፋሪ እና ልፋጭ ሥጋ ተኝታችሁ እየዋጣችሁ፤ ሰው የቀዳውን ውሀ እንዲሁም የወተት ጭላጭ እና አሬራ እየጠጣችሁ ወዛሞች ትሆናላችሁ እንጂ እንዴት እንደኛ አስቀያሚ መሆን ትችላላችሁ? ያውም ቢሆን አንድ ቀን የማታስፈልጉ መሆናችሁን ሲረዳ ጌታችሁ የት እንድሚጥላችሁ እንኳ አታውቁትም። እስከዚያው ይህን የምትጨፍሩበትን የተለያዩ ሰብሎችና የሚመረትባቸውን፣ የተለያዩ እንስሳት የሚረቡበትን አገር ሁሉ ከሌሎች ጠላቶቻችን ጠብቀን ስናቆይ ዱር እየዋልን ዱር እያደርን ሐሩሩ፣ ውርጩ፣ ረሀብ፣ ጥሙ ተፈራርቆብን ነው መልካችን አስቀያሚ መሆን የቻለው፣ ቆዳችንም የገረጣው፤ በዚህ ደግሞ እንኮራለን እንጂ አናፍርበትም። መልካችን ኑሮአችንን ይመስላል፤ የድካማችንን ውጤት ባንጠቀምበትም እንደናንተ ያሉ ውሾች እና ጌቶቻችሁ እየተጠቀማችሁበት ትገኛላችሁ፤ ታዲያ ባለውለታዎች በመሆናችን መጥፎ ስምና ስድብ ይገባናል?
ዉሻ፤ አገሩን ሁሉ የጠበቁት ሰዎች ናቸው እንጂ እኛ ነን ትላላህ እንዴ? በሌላ በኩል ደግሞ ተሰደን ኖርን ትላለህ፤ አታፍርም ስትዋሽ? ደግሞ የኛም አገር ባለቤት መሆን ያምራችኋል እንዴ? ጌቶቻችን አደላድለው ማድሪያችንን ስለሰጡን ከነሱ ጋር ሆነን ያላችሁበትንም አስለቅቀናችሁ መድረሻ ልናሳጣችሁ እንችላለን፡፡ ደግሞ ከፍተኛ የማሽተት ችሎታ ስላለን መረጃ በወቅቱ በማቀበልና የስዎችን ደህንነት በመጠበቅ በታማኝነት ስለምናገለግል ሰው ላደረገው የአገር ጥበቃ ሁሉ የኛም ከፍተኛ አስተዋጽኦ አለበት።
ዝንጀሮ፡ ይህን እንድትናገር የሚያደርግህ ሆዳችሁን እየሞላችሁ ለሰው ታማኝ ሆናችሁ መኖራችሁ አርቃችሁ እንዳታስቡ ስላደረጋችሁ ነው፤ ብታስትውሉ ኖሮ በየጊዜው አገር ምድሩን በሙሉ ሊወስዱት ከመጡ ወራሪዎች ተከላክለንና ተቆጣጠረን ባናቆየው ኖሮ አሁን ሰዎችና እናንተ የምትፈነጩበት ባላገር ሁሉ የሌሎች ፍጥረታት ግዛት ሆኖ ይቀር ነበር። እናንተም የቀብሮንና የተኩላን ያህል እንኳ ችሎታ ስለሌላችሁ ተበታትናችሁ ዘራችሁ ሁሉ ይጠፋ ነበር፤ ዉሾች የተባላችሁ ፍጡራን የምታደርጉትን አታውቁትም፤ የጌቶቻችሁን ጥፋቶች ማስፈጸም ሥራ ነው ትላለህ እንዴ? ማስተዋል ቢኖራችሁ ኖሮ ውለታችንን ታደንቁት ነበር። ስውም ለራሱ ጥቅም ሲል እየተጠቀመባችሁ ስለሆነ ያላችሁበት ሕይወት ጊዜያዊና አስተማማኝ አለመሆኑን መረዳት አልቻላችሁም፤ ብታስተውል ኖሮ ለታሠሩት ዉሾች ወገኖችህ ሁሉ ትቆረቆር ነበር፣ የልጆችህና ቤተስብህም እጣፋንታ ይኸው ስለሆነ አርቀህ ብታስብ ጥሩ ነው።
ውሻ፡- የምናደርገውንማ እናውቃለን፤ ይኸው ከናንተ በተሻለ ተንቀባረን መኖራችን አይታይህም እንዴ? ይልቅ ማንነትህን አውቀህ ወደጎሬህ ብትሄድ ይሻልሃል፡፡
ዝንጀሮ፡ አንተ ችሎ፣ ዘወትር እያሳደድከኝ መኖርህ ምን ያስደስትሃል? የምትጠብቀውን ይህን ሀብት ሁሉ ታየዋለህ እንጂ አታዝበትም፤ አትጠቀምበትም፤ ሰብሉንም እንደሆነ በፈቃድህ አትበላውም፤ ጌታሀ አንተን በየዱሩ ሲያንገላታህና ከኛ ጋር ሲያጣላህ ኖሮ በመጨረሻ ሁሉንም ምርት ከጎተራው አከማችቶ ሲሻው ይበላዋል፤ ሲሻው ሸጦና ለውጦ ይንደላቀቅበታል፤ ላንተ እንደሆነ ከፍርፋሪ በስተቀር የሚደርስህ ምንም ነገር የለም፤ ያችም ብትሆን ነፍስህን ለማቆየትና በቀጣዩ ደግሞ የጌታህን ከብቶችም ሆነ ሌሎች ፍጥረቶችን በንብረትነት ለመጠበቅ እንድትችል ወስፋትህን ለመሙላት ብቻ እንደሆነ አይታወቅህም?
ውሻ፡ እናንተ ዝንጀሮዎች ወይ አትቆፍሩ፣ ወይ አትዘሩ ወይ አታርሙ፣ ሰው ያበቀለውን እና ያመረተውን በአሳቻ ሰዓት እየሸመጠጣችሁ ከመብላት በስተቀር ምን ደግ ነገር ትሠራላችሁ? እያጠፋችሁ ከመኖር በስተቀር ምን ሥራ አላችሁ? እኛስ ጌቶቻችንን እያገለገልን እንኖራለን።
ዝንጀሮ፡ ተሳሳትክ፤ እኛኮ በአንድ በኩል ከእናንትና ከስዎች ጋር፣ በሌላ በኩል ከተፈጥሮ ጋር እየታገልን እራሳችንን ችለን ነው የምንኖረው፤ በጥርሳችሁና በአፋችሁ ጩኸት የምትኖሩ ስለሆነ የራሳችሁን ዕድል እንኳ የማታውቁ የስዎች ተቀጥላዎች ናችሁ፡፡ ጌቶቻችሁ ሲፈልጉ በሰንሰለት እያሠሯችሁ ወይም ኅሊናችሁ ተገድቦና ድምጻችሁ እንኳ እንዳይሰማ በሕይወት እያላችሁ በሳጥን ውስጥ ተቆልፎባችሁ ያለነፃነት ትኖራላችሁ፤ እኛ ዝንጀሮ የተባልነው ፍጡራን ግን ከአንድ ጫካ ወደሌላ ጫካ እየዞርን ተፈጥሮ የሰጠንን ፍራፍሪዎች እየተመገብን በነፃ እንኖራለን፤ ሰው ጫካውን እየመነጠረ ተፈጥሮ የሰጠንን እንዳንጠቀም ሲያደርገን ደግሞ ከአንድ ማሳ ወደሌላ ማሳ እየዞርን በሜዳ ላይ ያልተሰበሰበውን ሰብል ወይም ደግሞ ታጭዶ የተከመረውን ነዶ እየዘረጠጥን እንበላለን። ሰው እኛን የናቀው ሕንፃ ስለገነባ፣ ሀብት ስለሰበሰባና የጦር መሣሪያ ስለአከማቸ በዚያ ተመክቶ ይንቀናል እንጂ በተፈጥሮ እኩል ነን። እናንተ ነፃነታችሁን አሳልፋችሁ ህሊናችሁን ሸጣችሁ ለሆዳችሁ የተገዛችሁ ምቀኞች ባትኖሩ ኖሮ እኛ ሙሉ ነፃነት ኖሮን እንደናንተ ያሉትን እንሰሳት የተባላችሁ ጭቁን ፍጥረታት ጭምር ነፃ እናወጣ ነበር፤ አሁንስ ቢሆን በኑሯችን ብንጎሳቆልም እንደኛ ነፃነት ያለው የት ይገኛል? አንድ ቀን በጭቁን ፍጥረታት የተባበረ ትግል የሰው ኃይል ሲዳከም መድረሻ የምታጡት እናንተ ውሾች ናችሁ፡፡ ሰው የሠራውን ሕንፃ እያያችሁ በዘበኝነት ትጠብቃላችሁ እንጂ የናንተ ስላይደለ የምትተኙት ከስብሳብ፣ የምትበሉት ከወጭት አያልፍም፤ ይልቁንስ ብንስማማ አይሻልም? እናንተ እከብቶቻችሁ ጋ ሂዱ፤ ሰብል ሰብሉን ለኛ ብትተዉልን ምን አለ? ሰው ፍየል፤ በግ፤ ወይም ሌላ ሌላ እንሰሳዎችን ቢያርድ ምርጥ ምርጥ የሆነውን እንዲሁም ልብና ኩላሊት እንኳ ባይሰጧችሁም ሽንፍላና እንጀት እየበላችሁ ትኖራላችሁ። እናንተ ልክስክሶች ስለሆናችሁና የምትበሉትን እንኳ ስለማትመርጡ ተጸይፈዋችሁ ነው እንጂ ሰዎች እናንተንም ከመብላት አይመሱም ነበር።
ዉሻ፦ ሽንፍላም ሆነ ልፋጭ ትበላላችሁ የምትሉን እንደናንተ ሣርና የእንጨት ፍሬ ከመባላት ሳይሻል እንደማይቀር አጥተኸው አይመስለኝም፤ ዝናም ሲጠፋ ሣሩም ቅጠሉም ፍራፍሬውም ስለማይኖር በችጋር የምታልቁት እናንተ ናችሁ እንጂ እኛ አይደለንም። እኛ በታማኝነታችን ጦማችንን አለማደራችን አልታየህም፤ እናንተ ግን ዕድሜ ልካችሁን ስትሠጉ ነው የምትኖሩት፤ ታማኝ በመሆናችን ሳያበሉን የማያሳድሩን ሰዎች የሚሰጡንን ክብር አታውቀውም፤ እናንተ ድሮስ ማዕርግ የት ታውቃላችሁ?
ዝንጀሮ፦ አዎን የጌቶቻችሁ ዘበኞች ስለሆናችሁ ሆዳችሁ እንዴት ሊጎድልባችሁ ይገባል? ሆዳችሁ ከጎደለባችሁማ እንኳን ሮጣችሁ ልትናከሱ ቀርቶ ላንቃችሁ እንኳ መጮህ አይችልም፤ ይህን አገግሎት ካቆማችሁ ሰው እንደቆሻሻ እንደሚጥላችሁ አታውቁም? ሌላው ልታውቁት የሚገባው ደግሞ እኛ ተፈጥሮ የሰጠችንን ምንም ሳንለውጥ የምንመገብ ስለሆነ ስካር ወይም የእእምሮ መቃወስ የሚባል ነገር አናውቅም፤ ሰው ግን ብዙ የተለያዩ ምግቦችን ያለቅጥ እያግበሰበሰ፤ እየቀመመ ከተፈጥሮ ሕግ ውጭ እንደሱ ነፍስ ያላቸውን ፍጥረታት ሁሉ በግፍ እየገደለ ስለሚበላና ስለሚጠጣ አእምሮው ከመደንዘዙም በላይ ገሚሱ የማይድን በሽታ ይዞት ዕለተ ሞቱን እየተጠባበቀ በሥጋት የሚኖር ሲሆን፤ እናንተ ውሾችም ከሱ የተረፈውን ስለምትመገቡ የሰው በሽታ ይተላለፍባችኋል፤ አለቅጥ ለረዥም ጊዜ መተኛታችሁ በሽታ መሆኑ አይታውቃችሁም? እስቲ ምን የመኖር ዋስትና አላችሁ? ዕድሜያችሁስ ምን ያህል አጭር መሆኑን ተገንዝበኸዋል? እንደኛ በአካልም በአእምሮም ጤነኛ ሆናችሁ በነፃነት እንድትኖሩ የምንላችሁን ብትሰሙና ብትተባበሩ ይጠቅማችኃል፤ ለምሳሌ እንደኛው ያሉ ፍጥረታት የሚመስሉ የጋራ ጠላት ሆነው የሚያጠቁንን ጅቦች ለመከላከል ብንተባበር ከመጠቀም በስተቀር ምን ትጎዳላችሁ?
ውሻ፡ ጅብ በእርግጥ የሁላችንም ጭቁን ፍጥረታት ጠላት ነው፤ ሆኖም ጅቦችን መቋቋም የምንችለው እኛ ውሾች የተባልን ፍጥረቶች እንጂ እናንተ ምንም ማድረግ የማትችሉ ፍጥረቶች ናችሁ፤ እናንተ ጅቦችን ተዋጉ የምትሉት ለብልጠታችሁ ነው፤ እኛ ከጅብ ጋር ጦርነት ስንከፍት እናንት ሰብሉን ለመሸምጠጥ ዕድል እንዲኖራችሁ ስለሆነ ከናንት ጋር መተባበር አንችልም፤ አትቀልድ።
ዝንጀሮ፡ የተሳሳትከው አንተ ነህ፤ ጅብም ሆነ ሰው የናንተም የኛም ጠላቶች ናቸው፤ ሁለቱም ጠላቶቻችን ባይሆኑ ኖሮ በምድር ላይ የሚገኘው ተፈጥሮ በሙሉ ዱሩና ደኑ በሰዎች መመንጠሩ ሲቀርለት እየተስፋፋና እያፈራ ምድር በተፈጥሮዋ ተሞልታ የሁላችንም መመኪያ ትሆን ነበር፤ ደግሞ በየጫካው እየዞርን የፈለግነውን ተፈጥሮ የለገሰንን ሁሉ እንደልባችን እየተመገብን እንኖር ነበር። እኛ ዝንጀሮ የተባልን ፍጡራን ምንም እንኳ ዱር የምንኖር ቢሆንም፤ እንደናንተ በሰንሰለት ታሥሮና ለሰው በሪያ ሆኖ ከመኖር የተሻለ ሕይወት አለን፤ በዱር በገደሉ በየቁጥቁዋጦውና አረሁ ብንዘዋወርም ደኑ በኛ ቁጥጥር ሥር ስለሆነ ዋና ጠላታችን ከሆነው ሰው ነፃ ወጥተን እንደልባችን እየተዘዋወርን እንኖራለን፤ ሰው ደግሞ እኛን ለማጥቃት ቢዘምትም የምንበቀለው በድንገት በደፈጣ በምናደርገው ወረራ ነው፤ ዓመት ሙሉ የደከመበትን በአንድ ቀን ሌሊት የማውደም ልዩ ችሎታ አለን። ይህ በደፈጣ የምናደርገው ትግል የባላገር ባለቤት አድርጎናል፤ እናንተ ከጌቶቻችሁ ተለይታችሁ መኖር አትችሉም፤ አይፍፈቀድላችሁም፤ ወደዱር እንኳ ስትሄዱ ለሰው አሽከር ሆናችሁ ነው እንጂ ራሳችሁን ችላችሁ መሄድ አትችሉም፤ ምክንያቱም እናንተ የምትኖሩት ጌቶቻችሁን ለማገልግል ብቻ ስለሆነ ለሆዳችሁ የተገዛችሁ እንሰሳት ናችሁ። ሁሉንም ለራሱ ሊሰበስብ በሚያደርገው ጥረት ሰው እኛን ለመቋቋም የሚሞክረው በመሣሪያ ኃይል ብቻ ነው፤ ሆኖም፣ በጠመንጃ ሊገድለን ሲሞክር ባለን ከፍተኛ ወታደራዊ ቅልጥፍና ስለምንገለባበጥ ጥይት ሊመታን አይችልም፤ በየቦታው ከትሞ በየጊዜው አዳዲስ የመሣሪያ ክምችት እየጨመረ ያለው አቅም ስለሌለው ነው። ተባብረን ባላገሩን በሙሉ ብንቆጣጠርበት ሰው የሚያግበሰብሰውን ሀብት ሁሉ ያጣዋል፤ መሣሪያ የሚያገኝበት ምንጭ ይደርቃል፤ በመሣሪያ መጠቀም ካልቻለ ደግሞ በቀላሉ በእጃችን ሥር ወደቀ ማለት ነው።
አንድ ቀን ዝንጀሮ የተባለ ሠራዊት ሁላ ግምባር ከገጠመ እናንተ ውሾች ከጌቶቻችሁ ጋር መግቢያ አይኖራችሁም፤ እናንተ የምታመልኩት ሰው ሲጨፍርበትና ሲዘባነንበት የነበረውን ቤት ጥሎ ሲፈረጥጥ ከኛ እጅ አያመልጥም። እሱም የሠራዊታችን ተገዥ ይኖናል፤ ዛሬ ሰው የሚሰድበንና የሚንቀን ሁላችን በአንድነት ሆነን ፍርድ ስንሰጠው ነፃነት፤ እኩልነት፣ ፍትህ፣ ማለት ምን እንደሆነ ሰናሳየው፤ ዝንጀሮ መባላችን ቀርቶ እኛም የሰውን ክብር እናገኛለን፤ ይልቅስ የነፃነት ቀናችን እንዲፋጠን እኛ የምንላችሁን ብትሰሙን እና ብንደማመጥ ጥሩ ነው።
ውሻ፡ ከናንተ ጋር ሆነን ጅብን ልንዋጋ? ሞኛችሁን ፈልጉ! እናንተ ዝንጀሮዎች፤ ሰው ባያስጠጋንና በጫካ ብንኖር ኖሮ ዘራችን በጅብ ያልቅ ነበር፤ በየዛፉ ስለምትንጠላጠሉ ነው እንጂ እናንተ ነበራችህ የመጀመሪያዎቹ የጅብ ቀለቦች፤ ለመሆኑ ጅብ ምን ይበቃዋል? እነዚህን የዱር እንሰሳትም ሆነ የቤት እንሰሳትን ለመጨረስ አይመለስም። ስለዚህ አሁንም ይህች ሐሳብህ እኛ ዱር ገብተን በጅብ ስናልቅላችሁ እናንተ ያለተቀናቃኝ እንደልባችሁ የሰውን ሰብል ለመሸምጠጥ አይደል? ሰብል ደግሞ ተሽምጥጦ ካለቀ ሰው ለኛ የሚሰጠን ስለሚያጣ በረሀብ ማለቅ አንፈልግም፤ ስለዚህ ይህ ሐሳብህ ሌላ የብልጠት ዘዴ ስለሆነ እናንተን ማመን አይቻልም፤ እናንተ ለመሆኑ ምናችሁ ይታመናል? የወለዳችሁት ልጅና አባቱ እንኳ አይተመማኑም፤ እናት ዝንጀሮ ወንድ ልጇን የገዛ አባቱ እንዳይገድልባት ደብቃ ነው የምታሳድገው፤ ልጁም የአባቱን ኮቴ ሲለካ ሲለካ እያደገ አንድ ቀን ኮቴው ከአባቱ ኮቴ ጋር እኩል መሆኑን ሲያውቅ የጅር የበላይ ለመሆን አባቱን ከመዋጋት አይመለስም፤ እኛ ግን ውሾች የተባለን ፍጡራን ምንም እንኳን እናንተ ነፃነት የምትሉት ነገር ባይኖረንም ልጆቻንንና ወገኖቻችንን በጣም እናከብራለን፤ የተሰጠንን አክብረን እንበላለን እንጂ እንደናንተ ሠርቀን ወይም ዘርፈን አንበላም።
ዝንጀሮ፤ እንደናንተ ዝንጀሮ የሚባል ፍጥረት ጭላዳ፣ ጎመር፣ ወዘተ ተባብሎ በአፍና በዘር ተለያይቶ ሳይለያይ ከጦጣና ጉሬዛ ጭምር በሠራዊት በሠራዊት ተከፋፍሎ እየተመራ ነው የሚተዳደረው፤ እንደጉሬዛ ያለው በመንፈሳዊነት ይታወቃል፤ እንደአውራ ዶሮ ሊነጋ ሲል ደጋግሞ በመጮህ ፈጣሪውን ከማመስገኑም በላይ የቀኑን ምሥራች ለኛ ያበሥረናል፤ እያንዳንዱም ሠራዊት ወይም ጅር ደግሞ የየራሱን ባላገር ይቆጣጠራል፤ ታዲያ አንድ የዝንጀሮ መሪ በራሱ ሠራዊት ውስጥ ተቀባይነት ኖሮት መሪ መሆን የሚችለው ከማንኛውም ሌላ ዝንጀሮ ጋር ተፋልሞ ኃይለኛነቱንና ጀግንነቱን በተግባር አሳይቶ ነው እንጂ እንደናንተ ለማንም ጅራቱን እየቆላ አይደለም፤ ይህን ብታስተውል ኖሮ ጥያቄውን አትጠይቀኝም ነበር።
ዉሻ፤ በናንተ መካከል ዘወትር የሚታየውን ጠብ እና ጀብደኝነት ጀግንነት ትለዋለህ? እርስበርሳችሁ ባትጣሉ ኖሮ ለመሆኑ ምን አገር ይበቃችሁ ነበር? እኛስ ብንጣላ እንኳ ሰው በመካከላችን ገብቶ ጠበኛውን አሥሮ ስለሚያገላግለን አንጨነቅም፤ የምንጨነቀው ነገር ቢኖር አልፎ አልፎ በጭለማ ወጣ ወጣ ስንል ጅብ እንዳያጠቃን ብቻ ነው።
ዝንጀሮ፡ ሰውስ ከጅብ በምን ይለያል? ጅብ ጅብ የተባለበት ምክንያት እኮ ከመጠን ያለፈ ስለሚበላ ነው፤ እናንተ የምታመልኩት ሰው ግን መቼ በልቶ ይበቃዋል? ዘርፎ ዘርፎ እኛ ልንጠቀምበት እንችል የነበረውን ሁሉ የተፈጥሮ ሀብት ሰብስቦና አግብስብሶ በግል ሊጠቀምበት ከሚያስፈልገው በላይ እጅግ ያከማች የል? መች ይጠግባል? እንዲየውም ከሰው ጅብ ሳይሽል ይቀራል? ምክንያቱም ጅብ እኮ ከወገኑ ጋር ተካፍሎ ይበላል። እንደሰው ያለ ክፉ እንኳን ያለ አይመስለኝም፤ ጌታህ ብቻ ስለሆነ የማይገባውን ክብር ልትሰጠው አይገባም።
ውሻ፡ ታዲያ እናንተ ከሰው ይበልጥ ደግ ነን ነው የምትለው? ምንም ቢሆን ሰው ይሻለናል፤ የናንተና የኛ አኗኗር ለየብቻ ነው፤ ባላገሩን ለብቻው ከተማውን ለብቻው ተቆጣጥሮ የሚያስተዳድረው ሰው በሌለበት እንዴት እኛና እናንተ ተስማምተን መኖር እንቻላለን?
ዝንጀሮ፡ ቀስ እያልኽ አትጠጋኝ፤ እዚያው ባለህበት ቆይ፤ እናንተ ውሾች እኮ ከኛ ጋር በአንድ ቦታ ኑሩ አላልናችሁም፤ እናንተ የምትመገቡት ሌላ እኛ የምንመገበው ሌላ፤ እንደየልማዳችን ለየራሳችን መኖር የሚከለክለን ምንም ነገር የለም፤ እኛ የእናንተን ሳንፈልግ፤ በየቀያችን፣ እናንተም በየቀያችሁ እየኖርን፣ እናንተም የኛን ሳትፈልጉ በጋራ ጠላቶቻችን ላይ የጋራ አቅዋም ብንወስድ ማን ይጎዳል? በነዚህ ጠላቶቻችን ላይ ብንተባበር ጥንትም የራሳችን የነበረው ደኑ ተራራው፤ ሽንተረሩ ወንዛወንዙና የዱር ሀብቱ ሁሉ የናንተና የኛ የተናቅን እንሰሳት የተባልን ፍጡራን ስለሚሆን እናንተ የሚስማማችሁን እኛም የሚስማማንን እየተመገብን እናንተ እኛ ጋ ሳትደርሱ፤ እኛም የናንተን ሁሉ ሳንነካ የናንተም ሆነ የኛ ትውልድ ጦርነት አለብኝ በማለት ሳይጨነቅ በሰላም ተከባብረን መኖር እንችላለን።
ውሻ፤– አሁን ገና እውነት የምትናገር መሰለኝ። ስው እኮ እኛ ተዋግተን አንዳንዶቻችን ክፉኛ ቆስለንና ሞተን ከብቱንና ንብረቱን ብንጠብቅለትም ሰው የፈለገውን ይወረውርልናል እንጂ የደከምንበትን ከማየት በስተቀር አንጠቀምበትም፤ ጌታችን ሰው ከፈለገ ይሸጠናል፤ ይለውጠናል፤ በማናውቅበት አገር ከዘመዶቻችን ተለይተን ስዎችን ለመጥቀም ሰላማዊ ፍጥረታትን በማጥቃት ጠላት ከማብዛት በስተቀር ምንም መብት የሚባል ነገር አናውቅም። ረሀብና በሽታ እንኳን ሲያጠቃን የመዳን ተስፋ ስለሌለን ሞታችንን ብቻ ነው የምንጠቀው፤ እንደዚህ ባለው ኑሮ ከመካከላችን አንዱ ሲጎድል ወይ ሞቶ ወይ ተሽጦ መሆኑን ተረድተን ለዛሬ ከማሰብ በስተቀር የወደፊቱን ስለማናውቀው የያንዳንዳችን ቀን እስኪደርስ መስለን እንኖራለን ። ሌላው ነገር ደግሞ የእናንተ ኑሮ በየቁጥቋጦውና ገደላ ገደሉ የሆነው የተፈጥሮ ሀብታችሁ ስለተወሰደባችሁና ስለተሳደዳችሁ ምርጫ አጥታችሁ መሆኑን ተረድቻለሁ። ለካ ሁለታችንም ጭቁኖች ነን! ያውም የጋራ ጨቋኛችን በሆነው ሰው። የድሮውን የጥላቻ ታሪክ ትተን አሁን ያለንበትን ጭቆና በጋራ ለማስወገድ መተባበራችን የሚከፋ አይመስለኝም፡፡ ታዲያ እናንተ የኛን ሳተፈልጉ ወደኛ ሳትደርሱና እኛም ለራሳችን በሚስማማን ሁኔታ መኖር የምንችል ከሆነ ሊያስማማን ይችላል፤ ግን ሰው እኮ በጣም አዋቂና ከአቅማችን በላይ የሆነ መሣሪያ ስላለው እሱን ክደን እንዴት ሊሆንልን ይችላል?
ዝንጀሮ፦ አይ ችሎ ማደር እውነቱን መናገርህም ያሰመሰግንሃል፤ የዋህ መሆንህንም እረዳለው፤ ሆኖም እናንተ ውሾች የተባላችሁ ፍጡራን ሰው ካላሳደራችሁ ሕይወት እንደሌላችሁ ማመን የለባችሁም፤ ዋናው ነገር ይኸ ነው። በራሳችሁ ጥረት ለኑሮአችሁ የሚያስፈልጋችሁን ማግኘት እንደምትችሉ አንተ ራስህ አሁን ተናግረከዋል፤ እናንተ የቤት እንሰሳት የተባላችሁትና እኛ የዱር አራዊት የተባልነው ዝንጀሮዎች የአንደኛችን ወገን የሌላውን ወገን እንደጠላት አለማየታችን የመጀመሪያው ትልቅ እርምጃ ነው። ሰው በኛና በእናንተ ልዩነት ተጠቅሞ እናንተን በኛ ላይ እያዘመተ ነው ተንደላቆ የሚኖረው፤ ወደፊትም ዘራችን ከዘራችሁ ጋር ደም ተቃብቶ በጠላትነት ሲዋጋ ሰው ግን ተደላድሎ ለመኖር ነው የሚያቅደው። ወደፊት ከማሰብ ይልቅ ወደኃላ እያሰብን እና እየተጋጨን መኖር የለብንም፤ ድሮ ማ በማን ላይ የበለጠ ጉዳት አድርሷል የሚለውን ለማጣራት ብንሞክር አጣርተን ለማረጋገጥ ያስቸግረናል። እንደዚያ ብናስብ ቂምበቀል እየተወረሰ በናንተም በኛም ወገኖች መካከል ሳያቋርጥ እያጣላን ከሚኖር በስተቀር የሞቱትን አያስነሣም፤ ለወደፊቱም ሁላችንንም አይጠቅመንም፡፡ ዛሬ ያለንበትን ጭቆና በጋራ እናስወግድ ማለትህ ትልቅ እርምጃ ነው፡፡ ይህ የአስተሳሰብ ለውጥ ነው የድል በር የሚከፍትልን፡፡ አቋማችን አንድ ከሆነ እና እርስበርሳችን ላለመጣላት ከተስማማን የሰው መሣሪያ የትም አያደርሰውም፤ በመጀመሪያ ሰው የሚኖረው በኛ ልዩነትና ጠብ ላይ መሆኑን እንተማመን፤ ዘለዓለም እንሰሶች ተብለን አንኖርም፤ የእስከዛሬው ይበቃናል፤ በተባበረ ትግላችን ከሰዎች እኩል መሆናችን አይቀርም፤ ሆኖም በጋራ ለመታገል ቃለመሐላ መፈጸም አለብን። ከዚህ በኃላ ያለው ቀላል ነው።፡
ውሻ፦ እኛ እኮ እናንተን የምናሳድደው ጌቶቻችንን ፈርተን እነሱን ለማገልገል እንጂ እናንተ ዝንጀሮ የተባላችሁ ፍጡራን ምንም ልታደርጉን አትችሉም፤ ከናንተ ጋር መሠረታዊ ጠብ ሊኖረንም አይችልም፤ እኛ ከጌቶቻችን ነፃ መሆን ከቻልን በባላገር ውስጥ መኖር እናውቅበታለን፤ ከዘመዶቻችን መካከል ተኩላ የሚባል ዘር ከናንተ ጋር በጉርብትና እንደሚኖር ታውቃለህ። እናንተን ማሳደድ ስንተው ታዲያ ስው ወደባላገር እንዳይመጣ በመሣሪያው ተጠቅሞ ጉዳት እንዳያደርስብን ምን ማድረግ ይቻላል?
ዝንጀሮ፡ ቀበሮ “ሰውን ማመን ቀበሮ ነው” ያለችው ከናንተ ያነስ አቅም ያላትና የናንተው ወገን አይደለችም እንዴ ቤቷን ጫካ አድርጋ እንደኛ የምትኖረው? አትስጉ። በመጀመሪያ የውሻ ወገን ሁሉ ወራዳ ልክስክስ ተብሎ በመቃብርና ሕይወት መካከል እንዲኖር ሰው ለራሱ ጥቅም ያደረገው ተንኮል መሆኑን መረዳቱ ነው። ይህን ውሻ ለተባለ ፍጡር ሁሉ ማስረዳትና ማሳመን የናንተ ተግባር ይሆናል። ውሻ የተባለ ሁሉ ከትንሽ እስከትልቅ ሴትና ወንድ ሳይባል በሰንሰለት የታሠረውም ያልታሠረውም እንዲያምን ማድረግ አስፈላጊውን ጊዜ ወስዶ መሠራት ያለበት ትልቅ ሥራ ነው። ታዲያ ቀጥሎ በጋራ ተስማምተን አብረን እርምጃ ከመውሰዳችን በፊት ሴቶች ውሾችም ሆኑ ቡችሎች ተሳስተው አንዳች የጥላቻ ምልክት በጌቶቻቸው ላይ እንዳያሳዩ ጥንቃቄ መደረግ አለበት።
ውሻ፤– እኛ ወደን አይደለም ታማኝ ሆነን የምንኖረው፤ ምርጫ አጥተን ነው እንጂ፤ አብዛኛዎቻችን ጌቶቻችን ወደውጭ ለአገልግሎት ሊያሰማሩን ካልሆነ በስተቀር ወይ በር ተዘግቶብን ወይ ደግም በሰንሰለት ታሠረን ነው የምንኖረው፤ ታዲያ እንዴት የጋራ እርምጃ መውሰድ እንችላለን?
ዝንጀሮ፦ ዘዴማ ያስፈልጋል፡፡ ለምሳሌ በመጀመሪያው እርምጃ እኛ ስንመጣ እንድታጠቁን ይልካችኃል፤ በዚህን ጊዜ ጩኹና ስንሸሽ ተከሉን፤ ሰው እስከማይደርስበት ዱር ድረስ ያባረራችሁን መስላችሁ በመጨረሻ እንደደመሰስናችሁ ለመምሰል ሁላችሁም ድምፃችሁን አጥፉ፤ ይህን ጊዜ ሰው ያመፃችሁበት ሳይሆን ሞታችሁ ያለቃችህ ስለሚመስለው ሌሎች ውሾች ወገኖቻችሁን ማዝመቱ አይቀርም፤ በሁለተኛው ጊዜ ሲያሰማራችሁ ጩኸቱን እየቀጠለ ዉሻ የተባለ ሠራዊት ወደፊት ወደኛ በመገስገስ የበፊተኛውን እርምጃ እየደጋገመ ከወገኑ ጋር ይደባለቃል። እኛም ለሰው ጥይት ብቻ እንደማንሸነፍ ከዚህ በፊት እንደነገርኩህ በተለመደው የደፈጣ ውጊያ ስልታችን የተለያዩ የጥቃት እርምጃዎችን ስለምንወስድበት ሰው የሚመካበት ሰው-ሠራሽ ነገር ሁሉ እንደማያድነው ያየዋል። በምናደርገው የመረጃ ልውውጥ እና ስልታዊ አመጽ በየአቅጣጫው እንቅስቃሴያችን ሲበረታበት ትዋጉለት የነበራችሁ እናንተ ጭቁን ፍጡራን ሁሉ ትታችሁት ከገኛ ጋር ስትሆኑ መሣሪያውን መጠቀም እንኳ አቅቶት ብቻውን ይቀራል። እኛና እናንተ ጭቁኖች ሁሉ አንድነት ስንፈጥር ክዚህ ቀደም የምታደርጉት የሕይወት መስዋዕትነት ይቀራል። እነዚህ እርምጃዎች ተደጋግመው ሲፈጸሙ ሰው ብቻውን ስለሚቀርና አብዛኛዎቻችሁን ወደኛ ለማዝመት ሲል ስለሚፈታችሁ ነፃ እየወጣችሁ ባላገር ትገባላችሁ፤ እኛም ከናንተ ጋር በመተባበር ታሥረው የቀሩትን ባለን ጥበብ ዘምተን እንፈታቸውና የሰውን ገዥነት ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ እናስቀራለን፤ ከዚህ በኃላ ገዥና ተገዥ ሳይኖረን ሁላችንም ተከባብረን በሰላም እንኖራለን፤ ገባህ?
ውሻ፦ እውነት ነው፤ እኛ ከተባበርን ሌሎች ጠላቶቻችንን መቋቋም እንችላለን፤ ሰው የሚገለገልባቸውን በጎች፣ ፍየሎች፣ ወዘተ በማደን መኖር እናውቅበታለን።
ዝንጀሮ፦ ልብ በል፤ የናንተም ሆኑ የኛ ወገኖች በሙሉ እንዲቀባሉን እኛ ተንቀን የነበርንና በዚህ የነፃነት ጎዳና የተሠማራን ሁሉ የሌሎች የተናቁትን ፍጡራን መብትና ክብር በመጠበቅ ጥሩ ምሳሌዎች መሆን ይኖርብናል፤ አቅም አለን ብለን ደካማና አናሳ የሆኑትን የሆኑትን ፍጥረታት በፍጹም መጉዳት የለብንም፤ አንዱ ኃይላችን በሁሉም ወገኖች መታመናችን ነው፤ በተጨባጭ ጥሩ ምሳሌ እያሳየን ስንቀሳቀስ በየቦታው ውዳቂ መስለው የሚታዩት ፍጡራን ሁሉ የቆምንላቸው መሆኑን ሲረዱ በምናደርገው የጋራ እርምጃ ሁሉ በፍላጎታቸው ከጎናችን ይቆማሉ። ሁሉም ፍጡር አካባቢውን በነፃ ያስተዳደራል፤ የተናቁ ፍጡራን ሁሉ እንዳቅማቸው ለትግላችን ጠቃሚ አስተዋፅዖ ማድረግ ስለሚችሉ ሌሎች ፍጡራንን ሁሉ እንዳይጠላ ትንሹም ትልቁም ሴቱም ወንዱም የኛና የናንተ ወገን ሁሉ እንዲማር የማድረግ ኃላፊነት አለብን፤ አርስ በርስ በጠላትነት መተያየት ጨርሶ ቆሞ የሚቀጥሉት ትውልዶቻችን እኩልነትንና ፍቅርን ብቻ ማዳበር ይኖርባቸዋል።
ውሻ፦ የጋራ ጠላታችን የሆነውን የሰውንም መብት ማክበር አለብን ማለት ነው?
ዝንጀሮ፦ አዎን፤ የመጨረሻው ግባችን ሰውንም ነፃ ማውጣት ነው፤ እዚያ ደረጃ ላይ ለመድረስ ግን በሁላችንም በኩል የአስተሳሰብ ለውጡ የሠረጸ መሆን አለበት፤ በመጀመሪያ አሁን በላያችን ያለውን የገዥነት ኃይሉን በሙሉ አስወግደን ሰውን ከተራ ፍጡራን እኩል ማድረግ ብቻ ሳይሆን፤ እሱም ለዘመናት በራሱ ተመክቶ ሲፈጽም የነበረውን የገዥነት አቅሙ እና የበላይነት ሕልሙ ሁሉ ጠፍቶ ካለእኩልነት ሌላ የጋራ ጥቅም እንደሌለ የሚያምንበት ሁኔታ መፈጠር ይኖርበታል። ከላይ እንደገለጽኩልህ ሰው ራሱ አልፈጸመውም እንጂ የባህል ለውጥ የሚለውን በናንተና በእኛ የተናቅን ፍጡራን ብቻ ሳይሆን ሒደቱን ጠብቆ ሰውም ራሱ የባህል ለውጡን በተግባር እንዲፈጽም ይደረጋል።
ውሻ፦ አሁን በሁሉም ነገር የተግባባን መሰለኝ፤ ስለዚህ የጋራ ቃልኪዳናችንን በቃለመሐላ ማረጋገጥ እንችላለን።
ቃልኪዳን
- እኛ የተናቅን ፍጡራን ውሻ፣ ዝንጀሮ፣ ወዘተ እየተባልን በሰው እጅ ተጨቁነን መኖራችን የመነጨው ባለመተባበራችን መሆኑን ተማምነን ከዛሬ ጀምሮ አንደኛው ወገን ሌላውን በጠላትነት እንዳያይ፣ የአንደኛችን ወገን መጠቃት የሌላው ወገን መጠቃት እንደሆነ ተማምነን ኃይላችንን ሁሉ በጋራ ጠላታችን በሆነው ሰው ላይ አዙረን ባላገሩ በሙሉ በኛ በጭቁን ፍጥረታት ቁጥጥር ሥር እስከሚውል ድረስ ማንኛውንም መስዋዕትነት በመክፈል በተፈጥሮ ላገኘነው የጋራ ነፃነታችን ለመታገል ተስማምተናል።
- ዋናው የጋራ ጠላታችን ሰው መሆኑን ተረድተን ማንኛውም ሰውን የሚመለከት ምሥጢር ከመኻከላችን ሳይወጣ እንዲጠበቅ ማድረግ እንዳለብን ተስማምተናል። ለጋራ መብታችንና ኅልውናችን ስንል ማናቸውንም ጠላትን የሚመለከት መረጃ በወቅቱ ለመለዋወጥ ተስማምተናል።
- ዋናው ጠላታችን ማናቸውንም ጥቃት በአንደኛችን ወገን ላይ ቢፈጽም ሁላችንም ባለን አቅም ሁሉ በጋራ ለመከላከልና ብሎም በማጥቃት ይህን የጋራ ጠላታቻንን ለማንበርከክ ቆርጠን ተስማምተናል።
- በመካከላችን መከፋፈል እንዳይፈጠር፣ ሁላችንም ነቅተን ሕፃን፣ ሴት፣ ሽማግሌ አሮጊት ጎልማሳ ሳይቀር በዚሁ ጉዳይ እንዲያምኑ በየበኩላችን የዕለት-ተዕለት ከፍተኛ ዘመቻ ለማድረግ ተስማምተናል።
- በያለበት ያለው ጭቁን ፍጡር ሁሉ ለአንድ የጋራ ዓላማ መቆም የሚችለው ከልብ ሲከበርና ስለመከበሩም በተግባር ሲያይ ስለሆነ፣ በችግርና በውርደት መኖራችን እንዲቀርልን እንደምንፈልግ ሁሉ ፣ እንደኛ የተጨቆኑ ፍጡራንን በሙሉ መብታቸውን አውቀንላቸውና አክብረናቸው በጋራ ነፃነቱ መንገድ እንዲያምኑና ከጭቆናው ለመላቀቅ በውዴታቸው ከጎናችን እንዲሰለፉ የየበኩላችንን ጥረት ሁሉ ለማድረግ ተስማምተናል።
- ከዛሬ ጀምሮ ለዘመናት በመካከላቻን የነበረው ቂም ሁሉ እንዲቆም፤ አንዱ ወገን የሌላውን ዘር በመጥላት በጥላቻ ስም መጠራራታችን እንዲቀር፤ በየትኛውም ቀበሌና መንደር አንዱ የሌላውን ስም እንዳያጠፋ፤ ሁላችንም በየበኩላችን ለጋራ መብታችንና ክብራችን በመቆም ይህንንም አውቀን ልጆቻችንና በተሰቦቻችንን ለማስተማር ተስማምተናል።
- ከላይ ከተጠቀሱት ውስጥ እንደሁኔታው በሚያስፈልግበት ሁሉ በየኩላችን ዳይረክተሮችን፣ መምሪያዎችንና ቡድኖችን አቋቁመን እንዳስፈላጊነቱ ግንኙነቶችን በማድረግ ለመተባበር ተስማምተናል።
- አንዱ ወገን በሌላው ወገን ጣልቃ ሳይገባ፤ እያንዳንዳችን ወገኖች በውስጣችን ያለውን ጉዳይ በየራሳችን የውስጥ አመራር ለማስተዳደርና በውስጣችን አጥፊም ቢኖር በየራሳችን የውስጥ ሕግና ደንብ መሠረት እርምጃ ለመወሰድ እንደምንችል ተስማምተናል።
- እንደወንዝ ያሉትን የተፈጥሮ ሀብቶችና ከአንድ ዳር ወሌላ ዳር የሚወስዱ መንገዶችን በጋራና በእኩልነት የመጠቀም መብት እንዳለን ተስማምተናል።
- እኛ ዝንጀሮና ዉሻ የተባልን ጭቁን ፍጥረቶች ሰው እንደኛው ፍጡር መሆኑን አውቆ እስከዛሬ የፈጸመብንን በደል ተረድቶና ባደረገው ጥፋት ተጸጽቶ የሚያምንበት ደረጃ መድረሱን በጋራ ስናረጋግጥ በኛም ሆነ በማናቸውም ጭቁን ፍጥረታት ላይ ምንም ዓይነት ጥቃት ወይም የበቀል እርምጃ እንደማይወስድ ሲረጋገጥና ለፍትሕ ተገዥ ሲሆን፤ የሰው ዘር ሁሉ ከኛ ከጭቁን ፍጥረታት እኩል በነፃነት መኖር እንደሚችል እናምናለን።
“ሰውን ማመን ቀብሮ ነው”