Quantcast
Channel: ዘ-ሐበሻ – Ethiopian News | ዘ-ሐበሻ | Latest News Provider | News For All
Viewing all 8745 articles
Browse latest View live

የእውቁ ከያኒ ደበበ እሸቱ ‘ኢትዮጵያ የባሩድ በርሜል’መጽሐፍ ምርቃት በቶረንቶ ካናዳ |የጥሪ ማስታወቂያ

$
0
0


የጊዜውን የቅኝ ገዢዎች መላ ፍንትው ብሎ ያመላከተውንና በዘረኛው ጠበቃ በሮማን ፕሮቻዝካ በ1985 (እ.አ.አ) መግቢያ ላይ በጀርመንኛ ቋንቋ ተደርሶ በኦስትሪያ; የዓመቱ መጨረሻ ላይ በለንደን ከተማ በ እንግሊዙ ዓለም አቀፍ የዜና አገልግሎት በ እንግሊዘኛ ቋንቋ የታተመው ይህ መጽሐፍ በ እውቁ ከያኒ ደበበ እሸቱ ወደ አማርኛ ቋንቋ ተመልሶ ለንባብ በቅቷል:: ይህ ኢትዮጵያ የባሩድ በርሜል የተሰኘው መጽሐፍ የፊታችን እሁድ ከያኒ ደበበ እሸቱ በሚገኝበት ልክ ከዚህ ቀደም በዋሽንግተን ዲሲ እንደተመረቀው ሁሉ በቶረንቶ ካናዳም ይመረቃል:: በአካባቢው የምትኖሩ ሁሉ እንዳትቀሩ ተጋብዛችኋል – የመጥሪያው በራሪ ወረቀት የሚከተለው ነው::Debebe Eshetu Book Signing Poster

The post የእውቁ ከያኒ ደበበ እሸቱ ‘ኢትዮጵያ የባሩድ በርሜል’ መጽሐፍ ምርቃት በቶረንቶ ካናዳ | የጥሪ ማስታወቂያ appeared first on Zehabesha Amharic.


ሙፍቲ ሙሐመድ ሲራጅ አል አኒይ በመጨረሻም የአሏህን ጥሪ ተቀብለው አረፉ |ሳዲቅ አህመድ

$
0
0

Sheik

እኛም ካንተ፥ እኛም ወዳንተ ተመላሾች ነን!

የሰሜን አሜሪካ ኢስላማዊ ተቋማትን በመመስረት የመንፈስ አባት በመሆን ለአያሌ አመታት አግልግሎት የሰጡት አባታችን ሙፍቲ ሙሐመድ ሲራጅ አል አኒይ በመጨረሻም የ አሏህን ጥሪ ተቀብለው አረፉ። ሳዲቅ አህመድ በወርሃ ሜይ/2008 ከርሳቸዉ ጋር ቆይታ አድርጎ ነበር። አጠር ባለ መልኩ የተዘጋጀዉን ቃለ መጠይቅ ከታች ያንብቡ።ኢና ሊላሒ ወኢና ኢለይሒ ራጂኡን እኛም ካንተ፥ እኛም ወዳንተ ተመላሾች ነን።

 

ሶላተል ጀናዛ (ለሙታን የሚደረግ ጸሎት) የሚከናወነው በነገዉ እለት ዳረል ሒጅራ መስጊድ ዉስጥ ከሁለተኛዉ የጁመዓ (የአርብ) ሶላት በሗላ ነዉ። አድራሻ: 3159 Row St, Falls Church, VA 22044

 

የቀብር ቦታ:National Memorial Park

7482 Lee Hwy, Falls Church, VA 22042

 

ቆይታ ከሼህ ሙሐመድ ሲራጅ ሷል ጋር

 

እንደ ከዋክብት የደመቁ በድቅድቅ ጨለማ ውስጥ መንገድን አመላካች  ብርሃን የሆኑ አገርንና  ህዝብን ያቀኑ ህይወታቸውን በመማርና በማስተማር ሂደት ውስጥ ያሳለፉ አያሌ ኡለሞች (የሐይማኖት-ሊቃዉንት) በምድረ ሐበሻ መፈጠራቸው አሌ አይባልም።

 

ለዚህ  ሰናይ  ምግባር  እማኝ  ይሆን  ዘንድ  ፈርስት ሂጅራን ብሎም በድርን (የኢትዮጵያዉያን ሙስሊሞች ድርጅቶች) በመመስረት  የመንፈስ አባት ከሆኑት ከልጅነት እስከ አረጋዊነት ህዝብን እና አገርን ካገለገሉት  ሼህ  ሙሐመድ  ጋር አጭር ቆይታ አድርገን አንኳር የህይወት ተሞክሮአቸውን ጠየቅናቸው።መርሐባ በማለት የሚከተለውን አጫወቱን፦

 

ሳዲቅ፡በቅድሚያ የቤተሰብዎን ታሪክ ቢነግሩን?

ሼክ ሙሀመድ ሲራጅ: ቤታችን በይተል-ኢልም (የእውቀት ቤት) ነበር። ዓሊም ከነበሩት አባቴ ነው ብዙውን የተማርኩት። ሃብትም ነበራቸው። ብዙ የቀንድ ከብትና ግመሎች ነበሩን። አባታችን  ብዙ ደረሳወችን (የሀይማኖት ተማሪዎችን) ይቀልቡ ነበር።

 

ሳዲቅ፡ ዒልሙ (ሐይማኖታዊ ትምርት) የጀመረው ከርሶ  አባት ብቻ  ነው ወይስ አያት-ቅድመ-አያቶችዎም ዓሊም ነበሩ?

ሼክ   ሙሀመድ፡ የአባቴ  አባት ሳይሆን  አያታቸው

አሊም ነበሩ የአባቴ አባትም ቢሆኑ ሙእሚንና ፈጣሪን የሚፈሩ ነበሩ።

 

ሳዲቅ፡ የት ነው የተወለዱት?

ሼክ ሙሃመድ፡ የተወለድኩት ራያ ነው አውራጃው ማይጨው ራያ አዘቦ  ሲሆን  ወረዳውም ሙኸኒ ይባላል።

 

ሳዲቅ፡ መቼ ተወለዱ?

ሼክ   ሙሃመድ፡ የተወለድኩት ጃንዋሪ 15/1930 እንደ  አሮጳውያኑ አቆጣጠር ነው።

 

ሳዲቅ፡የመጀመሪያ  ልጅ ነዎት? እህትና ወንድም ነበሮትን?

ሼክ    ሙሃመድ፡  የአባቴ   የመጀመሪያ  ልጃቸው አብደላህ  ይባል ነበር። እኔ ሁለተኛ  ልጅ ነኝ። ከኔ በኋላ አሊ፤ ኢብራሂም፤ሙሃመድ፤ጁሃር እና ሃሺም የሚባሉ ወንድሞች ነበሩኝ በህይወት ያለው አሊ ብቻ ነው።

 

ሳዲቅ፡ ከርሶ ሌላ በዒልም  ውስጥ የገባ  ወንድም ነበሮት?

ሼክ   ሙሃመድ፡ቁርዓን  የቀሩ  ቢሆን እንጂ ዒልም እምብዛም የገቡ አልነበሩም።

 

ሳዲቅ፡ እድገትዎ  የት ነበር?  ዒልሙን የት በመሄድ አካበቱት?

ሼክ ሙሃመድ፡ ቁርዓንን ከአባቴ ራያ ተምሬአለሁ ወደ ደቡብ ወሎ እና ወደ የመን በመሄድም ተምሬAለሁ።

 

ሳዲቅ፡ ወደ የመን ሲሄዱ ስንት ዓመት ይሆኖት ነበር? የመንንስ እንዴት አገኟት?   የቋንቋስ ችግር ገጥሞት ነበርን?

ሼክ ሙሃመድ፡ ሃያ አራት ወይም ሃያ አምስት ዓመት ይሆነኝ ነበር የየመን  ሰዎች በጣም ጥሩዎች ነበሩ ተግባቢና ሰውን የሚረዱ ነበሩ በስራ ላይ ትጉህ ከመሆናቸው  ሌላ በጣም የተለየ ጥሩ ፀባይ ያላቸው ነበሩ። የቋንቋ ችግር አልነበረ ብኝም ገና አገሬ  ሳለሁ አረብኛን አውቅ ነበርና።

 

ሳዲቅ፡ ከየመንስ ሲመለሱ ወዴት ሔዱ?

ሼክ  ሙሃመድ፡ አባቴ አረፉ ልጆቻቸውን ትተው ሄዱ ወንድሞቼን ማሳደግና መቆጣጠር ስለነበረብኝ ወደ ስራ ዓለም ገባሁ። እርሻ እና ንግድን መከታተል ጀመርኩ።በከብት እርባታችን ውስጥ እስከ ሶስት መቶ የሚደርሱ ከብቶች ነበሩን። የልጆቹ እድሜ እስኪፀና ድረስ ለሰባት   መታት     መቆጣጠር ነበረብኝ።

 

ሳዲቅ፡ የቤተሰብን ሀላፊነት ከመወጣት ባሻገር ምን ያደርጉ ነበር?አ

ሼክ ሙሃመድ፡ አስተምርም ነበር ቢሆንም ከኔ በላይ ዒልምየነበራቸው ዓሊሞች በአከባቢያችን  ስለነበሩ እማርም ነበር።

ሳዲቅ፡ወንድሞቾ ካደጉ በኋላ የነበረው  ህይወቶ እንዴት ነበር?

ሼክ ሙሃመድ፡ የአገር ምርጫ ስለመጣ በአከባቢው ህብረተሰብ ለፓርላማ ተመርጬ እንደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር በ1954 ወደ አዲስ አበባ  ሔድኩኝ።

 

ሳዲቅ፡የፓርላማ ህይወቶ እንዴት ነበር?

 

ሼክ ሙሃመድ፡አላህ  አጅሩን  ይቁጠርልን  እንጂ ግዜው  በጣም አስቸጋሪ  ነበር።  አንዳንዶቹ ደካሞች ነበሩ ፓርላማ የመጡት  በባላባትነት እንጂ በእውቀት ባለመሆኑ፤  የሆነው  ቢሆንም አላህ ከኛ ጋር  ነበር። ቁርዓን በሬዲዮ እንዲቀራና ጁመዓን ለመስገድ እንዲፈቀድልን ጥያቄ ለንጉሱ አመራር ብናቀርብም ጁመዓ ከጉባዔ ወጥተን እንድንሰግድ፤በሮመዳን መንዙማና ዱዓ ከፉጡር በኋላ እንዲተላለፍ ተፈቀ ደልን። ከፓርላማው ስራም ጎን ለጎን የህግ ትምህርት ጀመርኩ በመጀመሪያ ሰርተፊኬት አግኝቼ በመቀጠልም በዲፕሎማ ለመመረቅ በቃሁ።

 

ሳዲቅ፡ ከዚያስ ፓርላማ ማገልገሉን ቀጠሉ ወይስ ወደ ዒልሙ ተመለሱ?

ሼክ ሙሃመድ፡ ወደ ፓርላማ አልተመለስኩም የአምባሳደርነት ሹመት Aግኝቼ ወደ የመን ሄድኩኝ።

 

ሳዲቅ፡ እንዴት አምባሳደር እንደተደረጉ ያው ቃሉ? ሼክ      ሙሃመድ፡ እኔ ምንም   የማውቀው ነገር አልነበረም አንድ  ቀን አንዋር መስጊድ ተሰባስበን የሀጅ ኮሚቴን እያቋቋምን ሳለን ከቤተ-መንግስት የተላከ ሻምበል እበርላይ ቆሞ  ጠራኝና  ከቤተ- መንግስት  እንደምፈለግ ነግሮኝ  በመኪናው  ይዞኝ ሄደ።  እንደ እኔ የተጠሩ    አምስትሰዎች     ነበሩ ሁላችንም ለምን ይሆን የተጠራነው ብለን መጨነቅ ጀመርን     የንጉሱ ተላላኪ              መጥቶ አይዞአችሁ የተጠራችሁት  ለደግ ነገር ነው ብሎ አጽናናን ከዚያ አንድ በአንድ እየተጠራን ማዕረግ ተሰጠን።

 

ሳዲቅ፡የመን በአምባሳደርነት ሲያገለግሉ ሁለቱን አገሮች በማቀራረብ ረገድ ምን ያደረጉት ነገር ነበር?

 

ሼክ  ሙሃመድ፡ በኢትዮጵያና በየመን መካካል ግኑኝነት ነበር ቢሆንም እኔ ከሄድኩ በኋላ  ያደረግሁት ነገር ቢኖር ግልጽ ያልነበረዉን የባህር ሀብታችንን ማካፈል ነው። በተጨማሪም ወንጀለኛን መለዋወጥ ማለትም የየመን ወንጀለኛ ኢትዮጵያ  እንዳይቀመጥ የኢትዮጵያ  ወንጀለኛ የመን ውስጥ እንዳይቀመጥ። ሌላው ብዙ ነው ትዝ አይለኝም።

 

ሳዲቅ፡ከየመን ሌላ በአምባሳደርነት የሰሩበት አገር አለ?

ሼክ መሃመድ፡ ስምንት ዓመት ከሰራሁ በኋላ   ወደ ካይሮ ግብፅ እንድዛወር ተወስኖ ሳለ ስራ ከመጀመሬ በፊት  የመንግስት   ለውጥ  መጣ። በደርግ ጥሪ ተደርጎልኝ ጓዜን ጠቅልዬ ወደ አዲስ አበባ ተመለስኩ በዉጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ዉስጥ የመካከለኛዉ ምስራቅ አገሮችን  እንዳነጋግርና  የመንግስትን  ፖለቲካ እንዳሰራጭ ስራ ተሰጠኝ።  ይህ በተጽዕኖ የመጣው የኮሚኒስት  ስርዓት  ለኢትዮጵያ አይመችም    ብዬ ኢትዮጵ ያን ለቅቄ ወደ የመን ሄድኩኝ ከዚያም ወደ ሳውዲ አረቢያ በመሄድ ለ13  ዓመታት ከተቀመጥኩ በኋላ  በስራ ምክንያት ወደ አሜሪካ መጣሁ።

 

ሳዲቅ፡ ወደ አሜሪካ እንዴት መጡ?

ሼክ ሙሃመድ፡መካ ያለው ራቢጠተል አለመል ኢስላሚያ (Muslim World League)   የተሰኘው ድርጅት ኒውዮርክ ባለው ቅርንጫፍ ቢሮው ስራ ሰጥቶኝ ነው የመጣሁት።

 

ሳዲቅ፡ ራቢጣ በሚሰሩበት ወቅት  ለኢትዮጵያ ሙስሊሞች የሚጠቅም ምን ያደረጉት ነገር አለ?

ሼክ  መሃመድ፡ የኢትዮጵያን ሙስሊሞች የሚመሩ ኡለሞች ክፍያ አልነበራቸውም በተለያዩ የአለማችን ክፍሎች ያሉ ኢማሞች ደሞዝ ሲኖራቸው የኢትዮጵያ ኡለሞች ደሞዝ የላቸውም። ለብዙዎቹ ደሞዝ እንዲከፈላቸው አድርጌአለሁ። ትምህርት ቤቶች እንዲሰሩ ጥያቄ  አቅርቤ ነበር ግን አልተፈጸመም። የራቢጣ ስራዬን በ1997 (እንደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር) ስጨርስ በብዙ ወንድምና እህቶች ጥያቄ ወደ ዋሺንግተን  ዲሲ መጣሁ። የኔው ከሆኑት ሙስሊሞች ጋር በመገናኘት ደዕዋ (ሰበካ) ማድረግ ጀመርኩኝ። በዓመት በዓል ካልሆነ የማይገናኙትን ሙስሊሞች መገናኘት በመጀመራቸው ቤት ተከራይተን ትምህርታችንን ቀጠልን።  ዛሬ  አለሀምዲልላህ  የራሳችን  መስጂድ ብሎም የራሳችንን ሬዲዮ ፕሮግራም ለማስተላለፍ በቅተናል።

 

ሳዲቅ፡ ስንት ልጅና የልጅ ልጆች አሎት?

ሼክ ሙሃመድ፡ አስራ አራት ልጆች አሉኝ።  ስምንት ወንድ ሰባት ሴቶች አስራ ስምንት የልጅ ልጆች አሉኝ።

ሳዲቅ፡ለመላው ኢትዮጵያውያን  የሚያስተላልፉት መልዕክት ካለ?

 

ሼክ ሙሃመድ፡ መልዕክቴም አደራችሁን አደራችሁንዲናችሁን(ሐይማኖታችሁን) አጥብቃችሁ ያዙ፤ እንደ ማዕበል ወደላይና ወደታች የሚማታ ነገር መጥቷል። ሃይማኖቱ አንድ ነው ቁራአንና ሃዲስን ቀጥ ብላችሁ ያዙ።በዘመናችን ወጣቱን ግራ የሚያጋቡ ሰዎች አሉ፤ ወጣቱ የሰራው መጥፎ ስራ የለም። ተጠንቅቃችሁ ቁርዓንና ሐዲስን ይዛችሁ እንድትራመዱ፤ እውነትን እንድትይዙ፤ ለሸይጣን እጃችሁን እንዳትሰጡ። ሀቅ በጣም መሪር ናት ጀግንነት ያለው ሰው እንጅ ሌላ አይወጣትም፤ ስለዚህ አደራ የምላችሁ ዲናችሁን አጥብቃችሁ ያዙ፤ ሞት አይቀርም፤ ይህች ታልፋለች።

 

The post ሙፍቲ ሙሐመድ ሲራጅ አል አኒይ በመጨረሻም የአሏህን ጥሪ ተቀብለው አረፉ | ሳዲቅ አህመድ appeared first on Zehabesha Amharic.

የመኢአድ የውጭ ጉዳይ ኃላፊ የነበረው አቶ አብርሃም ጌጡ ይግባኝ ተጠየቀበት

$
0
0

በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር

በአቶ ማሙሸት አማረ ካቢኔ የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) የውጭ ጉዳይ ኃላፊ የነበረው አቶ አብርሃም ጌጡ ህዳር 14/2008 ዓ.ም አራዳ ከፍተኛ ፍርድ ቤት (ሰባራ ባቡር) ቀርቦ ይግባኝ ተጠይቆበታል፡፡ የአራዳ ምድብ ችሎት ለህዳር 11/2008 ዓ.ም ቀጥሮበት የነበር ቢሆንም ህዳር 7/2008 ዓ.ም ፍርድ ቤቱ በነፃ እንዲለቀቅ መወሰኑ ይታወቃል፡፡

abreham getu

አቶ አብርሃም ጌጡ ሰኔ 12/2008 ዓ.ም ቤቱ ተበርብሮ ከታሰረ በኋላ 5ኛ ፖሊስ ጣቢያ ታስሮ ቆይቷል፡፡ ወደ ሶስተኛ ፖሊስ ጣቢያ ተዛውሮ ከቆየ በኋላ ከሀምሌ 12/2008 ዓ.ም ጀምሮ ማዕከላዊ ታስሮ ይገኛል፡፡ አቶ አብርሃም ጌጡ ‹‹በሽብር ወንጀል›› ለ6ኛ ጊዜ ፍርድ ቤት የቀረበ ሲሆን ከተያዘበት ጊዜ ጀምሮ በተለያዩ መዝገቦችና በተለያዩ ፍርድ ቤቶች ለ11ኛ ጊዜ መቅረቡን ጠበቃው ገልፀዋል፡፡

አቶ አብርሃም ጌጡ ወደ ማዕከላዊ ተዛውሮ ለሶስት ወራት በማዕከላዊ የቆየው ‹‹በሽብር ወንጀል›› ነው ተብሎ የነበር ቢሆንም ፍርድ ቤቱ የተከሰሰው በሽብር ሳይሆን በሀሰት ወሬ በማውራት በመሆኑ፣ ይህም ዋስትና እንደማያስከለክል፣ ለዚህ ክስም በቂ ዋስትና አስይዞ እንዲለቀቅ ወስኖ ነበር፡፡ ይሁንና አቶ አብርሃም ጌጡ ከእስር እንዲለቀቅ ፍርድ ቤቱ ከወሰነ በኋላም በማዕከላዊ እስር ቤት ታስሮ እንዲቆይ ተደርጎ ከሰባት ቀናት በኋላ ህዳር 14/2008 ዓ.ም ይግባኝ ተጠይቆበታል፡፡ ይህ ዜና እስከተጠናቀረበት ህዳር 16/2008 ዓ.ም ድረስ ‹‹የሀሰት ወሬ በማውራት›› በሚል ክስ ቀርቦበት እንዲፈታ የተወሰነለት አቶ አብርሃም ጌጡ በማዕከላዊ ታስሮ እንደሚገኝ ታውቋል፡፡

The post የመኢአድ የውጭ ጉዳይ ኃላፊ የነበረው አቶ አብርሃም ጌጡ ይግባኝ ተጠየቀበት appeared first on Zehabesha Amharic.

ልብ አንጠልጣዩ ‘ሞጋቾች’ድራማ ምዕራፍ 3 የዘገየበት ምክንያት ታወቀ

$
0
0

(ዘ-ሐበሻ) ልብ አንጠልጣዩና በርካታ ተከታዮችን ያፈራው ሞጋቾች የኢቢኤስና ዩቱዩብ ቴሌቭዥን ድራማ ምዕራፍ ሁለት ድንገት እንዲያልቅ የተደረገበት እና ም ዕራፍ 3ትም ቶሎ ያልጀመረበት ምክንያት ታወቀ:: ከደራሲው ኃይሉ ጸጋዬና ከፕሮዲውሰሯ መቅደስ ጸጋዬ የቅርብ ምንጮች ለዘ-ሐበሻ የደረሰው መረጃ እንደሚያመለክተው የድራማውን 3ኛ ክፍል የሚጽፈው ሌላ ደራሲ ይሆናል::

Hailu Tsegaye

Hailu Tsegaye

በፕሮዲውሰሯ መቅደስ ፀጋዬ (በድራማው የዶ/ር ኮከብን ገጸ ባህርይ ተላብሳ የምትጫወተው ) እና በደራሲው ኃይሉ ጸጋዬ መካከል በተፈጠረው አለመግባባት የተነሳ ደራሲው ካሁን በኋላ ድራማውን አልጽፍም በማለቱ ድራማው ሊዘገይ መቻሉን ያስታወቁት የዘ-ሐበሻ ምንጮች ም ዕራፍ 3ን (ከክፍል 49) በኋላ ያለውን ውድነህ ክፍሌ የተባለው ደራሲ እንደሚጽፈው አስታውቀዋል::

ደራሲ ኃይሉ ጸጋዬ ድራማውን ካሁን በኋላ አልጽፍም ያለበትን ምክንያት የዘ-ሐበሻ ምንጮች ሲያስረዱ “ፕሮዲውሰሯ (መቅደስ) በሥራዬ ውስጥ ጣልቃ እየገባች አስቸግራኛለች” በሚል ምክንያት ነው::

Mekedes Tsegaye

Mekedes Tsegaye

የማዕበል ዋናተኞች የራድዮ ድራማን ለረዥም ጊዜ በመጻፍ የሚታወቀው ደራሲ ሃይሉ ጸጋዬ ለ እረፍት የመጣ ፍቅር የተሰኘውን የኮሜዲ ትያትር ጨምሮ በርካታ የቴሌቭዥን; የራድዮ እና የመድረክ ድራማዎችን ጽፏል::

ሞጋቾች ድራማ ክፍል 49 (ምዕራፍ 3) በቅርቡ እንደገና ወደ ዕይታ ይመለሳል ይባል እንጂ መቼ እንደሚመለስ የታወቀ ነገር የለም::

ሞጋቾች ድራማ የመጨረሻው ክፍል 48 ከታየ አንድ ወር አልፎታል::

The post ልብ አንጠልጣዩ ‘ሞጋቾች’ ድራማ ምዕራፍ 3 የዘገየበት ምክንያት ታወቀ appeared first on Zehabesha Amharic.

የፕ/ር ብርሃኑ ነጋ ከአስመራ ወደ ብራሰልስ መጠራት

$
0
0

nega berehanu

ፕሮፌሰሩ ለረቡዕ ህዳር 22 ቀን 2008 ዓ.ም. (December 2, 2015) ከአስመራ ወደ ቤልጄየም ብራሰልስ የተጠሩት በሀገራችን ኢትዮጵያ ድርቅን ተከትሎ በተከሰተው ፖለቲካዊ የፖሊሲ ውድቀት ወለድ ርሃብ ጉዳይ ላይ ለአውሮፓ ህብረት ፓርላማ ንግግር፣ ምክክር እና ውይይት ለማድረግ እንደሆነ ይነገራል፡፡ የኢህአዴግ የ11 በመቶ የቁጥር ኢኮኒሚ ዕድገት ጋጋታ ገደል የከተተውና በምግብ ራሳችንን ችለናል መዝሙር ከአዳራሹ ነፋስ እንደወሰደው የሚያሳብቀው ከ15 ሚሊዮን በላይ ህዝብ በርሃብ አለነጋ ከመገረፍ አልፎ አስቸኳይ የምግብ ርዳት እንደሚያስፈልገው የተለያዩ ዓለም አቀፍ ተራድዖ ድርጅቶች እና የተባበሩት መንግሥታት ይፋ አድርገዋል፡፡

ይሄንን እውነታ ለመደበቅ መንግሥት ከፍተኛ ወጪ በማውጣት ለማስተባበልና በርሃቡ ወደተጎ ዜጎች አካባቢ ሚዲያ ድርሽ እንዳይል እና እንዳይዘገብ በውስጥ መመሪያ መተላለፉንም ከሰማን ሰነበትን፡፡

 

ይሄ ሁሉ የራስን የጥፋት ገመና ለመሸፈን ሲባል ህዝብ ርሃቡ ከእኛ ቁጥጥር ውጭ አይደለም ሲባል ለሀገሬው ዜጋ በቋንቋው ሲነገር፤ ለዓለም አቀፍ ለጋሽ ሀገሮች ደግሞ በእንግሊዘኛ በሀገሪቱ ከፍተኛ የርሃብ አደጋ መከሰቱን እና በሀገሪቱ የእርዳታ ማስተባበሪያ የጠገኘው እህል ከአንድ ወር እንደማያልፍ በመግለፅ ተማፅኖውን ማሰማቱን ቀጥሏል፡፡ ይህንን ስንሰማ የኢህአዴግ መንግሥት አስተዳደር ኃላፊነቱ ለነጮች ነው ወይስ ለኢትዮጵያውያን የሚል ጥያቄ ቢያጭርም ከተለመድ የተለየ ነገር ግን የለም፡፡ ለዓመታት የተለመደ የመረጃ (ዳታ) ጋገራ መግለጫና ፕሮፖጋንዳ በተጨማሪ በግልፅ መረጃ ለማፈን ከፍተኛ በጀት መድቦ መንቀሳቀስ ከጀመረ እነሆ ከ10 ዓመታት በላይ ሆኖታል፡፡ ልዕለ ኃያሏ አሜሪካም ብትሆን ከስርዓቱ ያላትን የፀጥታ ጉዳይ ትብብር (ወታደሮችን ለአላስፈላጊ እልቂት ማገዳ ካላት ስምምነት) አኳይ እንደ ጥሩ አጋር ብትቆጥርም የስርዓቱን አምባገነንነት፣ ዘረኛ አገዛዝ፣ ዴሞክራሲያዊ ተቋማት አለመኖር፣ የፍትህ እጦት፣ ሙስና እና ተጠያቂነት የሌለው አሰራር የሚከተለው ስርዓት እንደሆነ ልትሸሽገው አልቻለችም፡፡
ይሁን እንጂ የአውሮፓ ህብረት የተለመደ ሰብዓዊ እርዳታውን በስሱም ቢሆን መለገሱን ባያቆምም የምንጊዜም የስርዓቱ ቀኝ እጅ የሆኑት እንግሊዝ፣ ጣሊያን እና አየርላንድ እንደድሮ ለስርዓቱ ሰዎች ፊት መስጠቱን የቀነሱ ይመስላሉ፡፡ በዚህም ምክንያት ኢትዮጵያን በሚመለከት በአውሮፓ ህብረት አሊያም በአውሮፓ ኢኮኖሚ ቅንጅት የጋራ አባል ሀገሮች በኩል ውሳኔ እንዲያልፍ እየተደረገ መሆኑን እየታዘብን ነው፡፡ ወቅታዊውን ርሃብ ለማስታገስና ለተጎዱ ወገኖች የሚደረው ሰብዓዊ እርዳታ እንኳ እንደቀድሞ በቀጥታ ለመንግሥት ከመስጠት ይልቅ በእርዳታ መልክ የተሰጠው ገንዘብ በሌሎች በጎ አድራጎት ድርጅቶች በኩል በቀጥታ ለተጎጂዎች እንዲደርስ የሚያስችል አሰራር እየተከተሉ እንደሆነ የስርዓቱ አጋር አሜሪካ እና በቅርቡም ስውድን የወሰደችው እርምጃ አንዱ ማሳያ ነው፡፡ ይህ የሚያሳየው ስርዓቱ በተለያዩ ለጋሽ ሀገሮች እንኳ እምነት እንደታጣበት እና የተለመደው የመረጃ ጋገራ ሪፖርትና ጋጋታ ፋይዳቢስ መሆኑን የተገነዘቡ ይመስላል፡፡
እነሆ አሁን ደግሞ የኢትዮጵያውን ርሃብ በተመለከተ ህዝባዊ ዓመኔታና ቅቡልነት ባይኖረው ኃላፊነት ያለበት መንግሥት እያለ ስርዓቱን ለመገርሰስ ከሚታገሉት መካከል ተዓማኒና ትክክለኛ መረጃና ትንታኔ ይሰጣሉ ተብለው ከታመኑት መካከል በአውሮፓ ህብረት ፓርላማ አማካኝነት ከአስመራ የትግል ሜዳ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ተጋብዘዋል፡፡ በርግጥ ፕሮፌሰሩ ካላቸው የፖለቲካ ስብዕና በተጨማሪ በሙያቸው ከፍተኛ የምጣኔ ሃብት ባለሙያና ተመራማሪ እንደመሆናቸው መጠን በስፍራው መጋበዛቸው የህብረቱ ትክክለኛ ምርጫ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡ ይሄ ደግሞ የስርዓቱን ሰዎች የበለጠ ምክንያታዊ መሸሸጊያ የሚያሳጣ ወቅታዊ የመረጃ ጉዳይ ሆኗል፡፡ የሚገርመው በኢትዮጵያ ስም ስርዓቱን ወክሎ በቤልጀየም ከፍተኛ ባለሙሉ ስልጣን አምባሳደር እያሉ ስለ ኢትዮጵያ ወቅታዊ ጉዳይ መረጃና ትንታኔ እንዲሰጡ ከበረሃ የትግል ሜዳ የፕሮፌሰሩ መጋበዝ ለስርዓቱ ትልቅ ራስምታት ነው፡፡ ምክንያቱም ፕሮፌሰሩን እና የሚመሩትን የፖለቲካ ድርጅትና አባላት በሽብርተኝነት ለማስፈረጅ ለዓመታት በተለመደ የመረጃ ጋገራ ቢሞከርም በአሜሪካም ሆነ በአውሮፓ ህብረት አባል ሀገራት ተቀባይነት አላገኘምና፡፡

Birhanu nega photo
በተለይ በመረጃ እና ሐሳቡን ለመግለፅ ለታፈነው የኢትዮጵያ ህዝብ ትልቅ አጋጣሚ ሲሆን፤ ለፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ እና ለሚመሩት ድርጅት እንደ አንድእመረታ ሊታይ ይችላል፡፡ እንደ አንዳንድ የስርዓት ቅርበት ያላቸው ምንጮች ጥቆማ ከሆነ መንግሥት ርሃቡን ከሀገሬው ሰው በመደበቅ ለጋሽ ሀገራት በተማፅኞ በማጨናነቅ ዕርዳታቸውን በጥሬ ገንዘብ ወይም ዶላር እንዲሆን እየሰራ እንዳለ እና ለዚህም ያቀረበው ምክንያት ገንዘቡ ከተሰጠኝ ከሀገር ውስጥ ነጋዴዎች እህሉን ራሴ ገዝቼ በማከፋፈል ጊዜና ጉልበት መቆጠብ እችላለሁ ማለቱ ተሰምቷል፡፡

ይህ ለተጎጂዎች ታስቦ ሳይሆን መንግሥት በሀገሪቱ ከደረሰበት ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ እጥረት የተነሳ አጋጣሚውንም እንደ ጥሩ ዕድል ሊጠቀምበት እንዳሰበና እስካሁንም እንዳልተሳካለት ለስርዓቱ ቅርበት ያላቸው ምንጮች ተጠቁሟል፡፡ በአሁን ወቅት ከአስከፊው ርሃብ በተጨማሪ በሀገሪቱ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሪ እጥረት በመከሰቱ የተለያዩ አስመጪዎች እና ኢንዱስትሪዎች ለአብነትም ቴክኖ ሞባይል የስልክ መገጣጠሚያን የመሳሰሉት ስራ ማቆማቸውም መነገር ከተጀመረ ሰነባብቷል፡፡ በዚህ ሁሉ የስርዓቱ አጣብቂኝ ውስጥ ፕሮፌሰሩ የበለጠ ተዓማኒነትና ተቀባይነት አግኝነተው በአውሮፓ ህብረት መጋበዛቸው በቀጣይ ምን ሊያሳየን ይሆን የሚለውን ወደፊት አብረን የምናየው ነው ሚሆነው፡፡

 

ቸር ወሬ ያሰማን፡፡

The post የፕ/ር ብርሃኑ ነጋ ከአስመራ ወደ ብራሰልስ መጠራት appeared first on Zehabesha Amharic.

የሴም ዘር ማን ነው? የኩሽ ዘርስ የቱ ነው? ሐበሻ የሚባሉትስ  እነማን ናቸው? |ከተማ ዋቅጅራ

$
0
0

ኢትዮጵያ ውስጥ አንዱ ከአንዱ የተለያየን አድርጎ ማቅረብ አሁን አሁን በሰፊው እየተሰማ ነው። ኢትዮጵያ ብዙ የሚባሉ የታሪክ ሙሁራን ቢኖራትም ሙህራኑ በአገር ጉዳይ በያገባኛል መንፈስ በአንድነት ተሰባስበው ከመመካከር እና ከማስተማር ይልቅ ዝምታን መርጠዋል። የኢትዮጵያን እውነተኛውን ታሪክ ለህዝባቸው ከማሳወቅ ችልተኝነት ማሳየታቸው ኢትዮጵያ እንድትፈራርስ እየሰራ ያለው ወያኔ ያስደስት ይሆናል። ወያኔ አሁን አሁን እየተከተለ ያለው የአረብ አብዮትን ነው። አረቦች ጥያቄአቸው እንዲመለስላቸው የሚፈልጉት በሁከት ነው። ግዛታቸውንም ማስከበር  የሚፈልጉት በሁከት ነው። ሃሳባቸውን ሌላው እንዲቀበላቸው የሚፈልጉት በማስፈራራት እና በሁከት ነው። እየገደሉ ሞተብን ብለው ይጮሃሉ እያፈነዱ አፈነዱብን ብለው ይናገራሉ በሁሉ ነገር በደል ፈጻሚ ቀዳሚዎቹ እነሱ ሆነው ሳለ ምላሽ የሚሰጣቸውን አገር አረብን ሊያጠፋ ነው ብለው ሁሉም እንዲነሱላቸው ማሳደም መቀስቀስ ይጀምራሉ አንድ ችግር ሲያጋጥማቸው ይሄንን ያደረሱብን እንደዚህ የምትባል አገር  እና እንደዚህ የተባሉ  አገር ናቸው ብለው በራሳቸው የተፈጠረውን ጥፋት ከማመን ይልቅ ወደሌላ አገር ላይ በመለጠፍ አረብ አገር በሙሉ እና ወዳጅ አገሮታቸውን ጥላቻ እንዲቀረጽባቸው አድርጎ  መመረዝ ነው። ወያኔም እየሄደበት ያለው አካሄድ ይሄንኑ ነው።

ethiopia

ኢትዮጵያ መሽቶ በነጋ ቁጥር አዳዲስ ነገሮችን የሚሰማባት አገር ሆናለች። እድሜ ለወያኔ በዘር ፐውዞ ፐውዞ አንተ አበሻ ነው እኔ አበሻ አይደለሁም። አንተ ሴም ነህ እኔ ኩሽ ነኝ። አንተ እንደዚህ ነህ እኔ እንደዚ አይደለሁም። አንተ ከገሌ ወገን ነህ እኔ ከእገሌ ወገን አይደለሁም  የሚል ጫጫታ በስፋት እየተሰማ ይገኛል። ይህም የሆነበት ዋናው ምክንያት የተማረው እና ታሪክ ጠንቅቀው የሚያውቁት ሙህራኖች በአንድላይ ተሰባስበው ስለ አገር በማሰብ የተለያዩ  መድረኮችን በመፍጠር  እውነተኛውን ታሪካችንን  ከማስተማር እና ከማሳወቅ ይልቅ ዝምታን በመምረጣቸው የተነሳ ወያኔ እና መድረኩን የፈቀደላቸው  የማያውቁትን ታሪክ  የየራሳቸውን ሃሳብ በማንጸባረቅ በተደጋጋሚ እየተነገረ  እና በመጽሃፍም ጭምር እውነትነት የሌለው ታሪክ አስመስለው እየተጻፉ በመሆኑ እንደዚህ የተዛቡ ታሪኮች ሲነገር በአጉል ተስፋ ሰዎችን ስለሚሞላቸው የኢትዮጵያን ታርክ የኛ ታሪክ አይደለም ብለው እስከማመን እያደረሳቸው ነው። በዚህ የተነሳ የኛ ታሪክ ወድቋል፣ ጠፍቷል፣ ተሰርዟል፣ ተረግጧል…… ሌላም ሌላም እየተባለ ስለሆነ  እውነተኛ ታሪክን እያፋለሱ ያሉትን ሰዎች ወደ ሚዲያው በማውጣት ከታሪክ ሙሁራኑ ጋር ፊት ለፊት በማገናኘትና   በማነጋገር ኢትዮጵያን የማዳኑን ስራ ትሰሩ ዘንድ ጋዜጠኞች ትልቅ ድርሻም አደራም አለባችሁ።

ሴም ወይንም ሴሜቲክ ማን ነው? ኩሽ ወይንም ኩሸቲክ ማን ነው? ሐበሻ የሚባሉትስ እነማን ናቸው? የሚለውን እንመልከት

ኖህ፡- ሴም፣ ካም፣ እና ያፌትን ወለደ ዘፍጥረት ፲+ ፩-፴፪ (10+1-32)

ሴም፡- ኤላም፣ አሦር፣ አርፋክስድ፣ ሎድ፣ አራም፣ ቃይናን ወለደ።

ካም፡- ኩሽ፣ ምስራይም፣ ፍጥ፣ ከነዓን ወለደ።

ያፌት፡- ጋሜል፣ ማጎግ፣ ማዴ፣ ያህያን፣ ያልሳ፣ ቶቤል፣ ሞሳሕ፣ ቴራስን ወለደ።

ከላይ የዘረዝርኳቸው የኖህ ልጆች እና የኖህ የልጅ ልጆች የሆኑ ናቸው።

ዛሬ ኢትዮጵያ ውስጥ በከፍተኛ ሁኔታ በሆነ የዘር መጠላለፍ የሚታየው ይሄንን እውነት ካለመረዳት ነው። ሴም በሉት ሴመቲክ ኩሽ በሉት ኩሸቲክ ለሴም አባቱ ለኩሽ አያቱ የሆነው ኖህ ነው። ታዲያ የአንድ ዘር ግንድ የሆንን ወንድማማቾች ይሄንን ያህል መጠላላት እና መለያየት ለምን አስፈለገ? ዛሬ ሴሜቲክ ነን እያልን የምንፎክር ዛሬ ኩሸቲክ ነን ብለን የምንፎክር አባታችን አንድ እንደሆነ  ሲነገረን መደምደሚያችን ኖህ እንደሆነ ስናውቅ ምን ይሆን መልሳችን። ከየት ተነስተን ወደ የት ነው የምንሄደው? ወዴየትስ ነው መሄድ የምንፈልገው? ከማንስ ተፈጥረን ነው የሌላ ነን የምንለው ዛሬ እኛ ሴም ነን እኛ ኩሽ ነን ብለን የምንናገረው የተፈጥሮ  ዑደታችን እውነቱ ይሄ ነው። ለዚህ ነው ብንጣላ የማንኮራረፈው ብንሰዳደብ የማንራራቀው የአንድ ቤተሰብ ልጆች ስለሆንን ነው። ነገሮችን ጠለቅ ብለን ስናውቅ ማንነታችንን እናውቀዋለን ማንነታችንን ስናውቅ ታሪካችንን እንወዳለን ታሪካችንን ስንወድ አገራችንን እንገነባለን አገራችንን ስንገነባ ለአለም ሁሉ የፍቅር፣ የሰላም የአንድነት የስልጣኔ መሰረት ሆነን እንታያለን።

ሌላው ሐበሻ ሴሜቲክ ናቸው እንጂ ኩሸቲክ አይደሉም ይሉናል። ከመነሻው እንዳየነው ሴም ለኩሽ አጎቱ ነው የኩሽ አባት እና ሴም  ወንድማማቾች ናቸው ማለት ነው። በቃ የኛ አመጣጥ እዚህ ጋር በአራት ነጥብ ተዘግቷል። ኩሸቲክ እና ሴመቲክ የአንድ ዘር ልጆች ነን። ታዲያ ሐበሻ የሚለው ቃል የመጣው ከየት ነው? ከተባለ መልሱ ከአረቦች ነው።

ነብዩ መሃመድ ከቆሬሾች ጋር ከፍተኛ ችግር ውስጥ በነበረበት ወቅት በጃፋር መሪነት የነብዩ  የቅርብ ሰዎች የነበሩትን  ወደ ኢትዮጵያ ሲልኩ የተናገሩትን ቃል እጠቅሳለው ቃሉ ቃል በቃል ከቁርአን ነው የተወሰደው << ሐበሻ (ኢትዮጵያ) የእውነት አገር ናት በውስጧም ሰውን የማይበድል እርሱም ዘንድ አንድም የማይበደል ንጉስ አለና ወደዚያ ብትሄዱ መልካም ነው>> ይላል። ነብዩ መሃመድ በእስልምና እምነት አማኞች ዘንድ ትልቅ ቦታ ያላቸው ሰው  ናቸው። ሐበሻ የሚለውን ስም እስካሁንም ድረስ አረቦች ይጠቀሙበታል። ታዲያ በነብዩ  መሃመድ እንዲህ የተገለጹት ደግ በደልን የማያደርጉ ህዝብን የማይበድሉ መሪ ኢትዮጵያ ነበራት። እኚህ መሪ የሴምም የኩሽም ልጅ የሴምና የኩሽ ሃረግ የነበራቸው መሪ ናቸው እንጂ ዛሬ ዛሬ እንደሚነገረው የወያኔ ፖለቲካ እና የወያኔ አካሄድ የሚከተሉ እንደሚሉት ሐበሻ ስለተባሉ የሴም ወገን ናቸው ተብሎ መነገሩ የራስን ታሪክ ጠንቅቆ ካለመረዳት እና የፖለቲካን ትርፍ ለማግኘት ተብሎ ታሪክን በገዛ ፍቃድ እንደመጣል ይቆጠራል። ለኢትዮጵያ የሚሰጥ የታሪክ፣ የጀግንነት፣ የስልጣኔ፣ የሃይማኖት፣ የስነ ፈጠራ፣ የባህል፣ የቋንቋ፣ ድርሻ የሴምም የኩሽም እኩል ታሪክ ነው። ማንም ከማንም የተነጠለ ታሪክ የለንም። ማንም ከማንም የሚለያይ ስራም የለንም። ወያኔ ለአገዛዙ ማቆያ ለስልጣኑም ማራዘሚያ በማሰብ መጀመሪያ እና መሃል የሌለው ጫፍ ብቻ ያለው ታሪክ ይነግረናል። ጫፉ ላይ ወጥተን ከማንነታችን ውጪ ግዜአዊ የፖለቲካ ትርፍ ፍለጋ ማንነታችንን እና አገራችንን አደጋ ላይ መጣል ተገቢ አይደለም ነገም ታሪክ ይጠይቀናል ማንም ከተጠያቂነት አያመልጥም። ስለዚህ ወደ እውነተኛው ማንነታችን መመለስ ያስፈልገናል።

እንደ ማሳሰቢያ መናገር የምፈልገው አንድ ሰው የተለየ ሃሳብ ለምን አመጣ ተብሎ አይከለከልም ማንም የፈለገውን ሃሳብ ማምጣት ይችላል ያንን ሃሳብ ግን በማስረጃ ሊያቀርብ ያስፈልጋል። በነጻ ሚዲያ ዘርፍ የተሰማራችሁ ጋዜጠኞች በታሪክ ዙሪያ የተለየ ሃሳብ ያለው ሰው ካለ ወደሚዲያው በመጋበዝ ከታሪክ ሙሁራኑ ጋር ግልጽ ትንታኔ ከሁለቱም ወገን እንዲሰጡበት በማድረግ እና ጥያቄአቸውን በማስረጃ እንዲመልሱ በማድረግ እውነታውን ህዝቡ እንዲያውቀው የማድረጉን ስራ ቢሰራ በህዝቡ ዘንድ የሚኖሩትን ብዥታዎች ያጠራዋል። ህዝብን በመከፋፈል ዙሪያ ወያኔ የሚጠቀምበትን መንገድ አንድ አንዶችም በመከተል ላይ ስለሆኑ የፈረሰውን በመገንባት የሃሰት ታሪካዊ ወሬዎችን እውነተኛ በሆነው ታሪክ በማነጽ ያስፈልጋል። ጥያቄ አንሺውን እና ሙሁራኑን በማገናኘት በየግዜው ትንታኔ እንዲሰጥበት በማድረግ  በጋዜጠኝነት ሙያውስጥ ያላችሁ ኢትዮጵያዊ ሁሉ ለአገራችሁ ታሪክ ስሩ።  ኢትዮጵያን ወደ ሰላሟ እና ወደ እረፍቷ የሚያመጣት መልካም መንገድ ነውና።

ከተማ ዋቅጅራ

26.11.2015

Email- waqjirak@yahoo.com

 

The post የሴም ዘር ማን ነው? የኩሽ ዘርስ የቱ ነው? ሐበሻ የሚባሉትስ  እነማን ናቸው? | ከተማ ዋቅጅራ appeared first on Zehabesha Amharic.

ዘ-ሐበሻ ኖቬምበር 5 ቀድማ በዘገበችው መሰረት ፖሊስ ዛሬ ለፍርድ ቤት መምህር ግርማን በግድያ ወንጀል እጠረጥራቸዋለሁ አለ

$
0
0

Memhir girma

(ዘ-ሐበሻ) ኖቬምበር 5 ቀን 2015 ዓ/ም “መንግስት በመምህር ግርማ ላይ ከግድያ ወንጀል ጋር በተያየዘ ተጨማሪ ክስ ሊመሠርት መሆኑ ተሰማ” በሚል ምንጮቿን ጠቅሳ መዘገቧ አይዘነጋም:: (የኖቬምበር 5ቱን ዘገባ ለማንበብ እዚህ ይጫኑ) አስተማማኞቹ የዘ-ሐበሻ ምንጮች ለዘ-ሐበሻ ያንን መረጃ ከሰጡ በኋላ በተለይ ፖሊስ መምህር ግርማን በነጋታው በዋስ ሲለቃቸው አንዳንድ ሰዎች በዘ-ሐበሻ ዘገባ ላይ ጥርጣሬ አድሮባቸው ነበር:: አንዳንዶችም በስልክ እየደወሉ “እንዴት ያልሆነ ነገር ትዘግባላችሁ” ሲሉ አስተያየት ሲሰጡን ነበር:: የኛ ምላሽ “ሁሉን በት ዕግስት ጠብቁ” የሚል ነበር:: ዛሬ ፍርድ ቤት የቀረቡት መምህር ግርማን ፖሊስ በግድያ ወንጀል እጠረጥራቸዋለሁ ማለቱን መንግስታዊ ሚድያዎች ዘግበዋል::

በተለይ የሕወሓት የመረጃ መረብ የሆነው ራድዮ ፋና ስለዛሬው የመምህር ግርማ የፍርድ ቤት ውሎ ያቀረበውን ዘገባ እንደወረደ አቅርበናል::

________________

ፖሊስ መምህር ግርማ ወንድሙን በተጨማሪነት በግድያ ወንጀል መጠርጠሩን ገለጸ

አዲስ አበባ ፣ ህዳር 17፣ 2008 (ኤፍ.ቢ.ሲ) መምህር ግርማ ወንድሙ በተጠረጠሩበት የማታለል ወንጀል የተፈቀደው ዋስትና ላይ የመርማሪ ፖሊስ ይግባኝ ውድቅ ተደረገ።

የአዲስ አበባ ፖሊስ የምርመራ ቡድን ከተጠርጣሪው ቤት ያገኘሁት ስምንት ሲም ካርድ ላይ እንዲጣራ ለኢትዮ ቴሌኮም ልኬ ውጤት እየጠበኩ ነው፤ ሌላ ተጠርጣሪም ስላለ ያን ለመያዝ የ14 ቀን የጊዜ ቀጠሮ ይሰጠኝ ቢልም የፌደራል የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት የተጠየቀው የምርመራ ስራ ተጠርጣሪውን ዋስትና የሚያስከለክል አይደለም በማለት ዋስትና መፍቀዱ ይታወሳል።

ይሁን እንጂ መርማሪ ቡድኑ ይግባኝ ጠይቆ ዋስትናውን በማሳገድ በፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ ችሎት ቀርቦ ተከራክሯል።

ችሎቱ የሁለቱን ወገን ክርክር መርምሮ ፖሊስ የተሰጠው ጊዜ በቂ ነው፤ ቀሪ ምርመራውን ለማድረግም ተጠርጣሪውን ዋስትና የሚያስከለክል አይደለም ሲል የተፈቀደውን ዋስትና አጽንቶታል።

በዚህም መምህር ግርማ በተጠረጠሩበት የማታለል ወንጀል በ50 ሺህ ብር፣ በሀሰተኛ ሰነድ በመገልገል ደግሞ በ40 ሺህ ብር በጠቅላላው የ90 ሺህ ብር ዋስትና ተፈቅዶላቸዋል።

በተያያዘ የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን የምርመራ ቡድን መምህር ግርማ መንድሙን ከዚህ በፊት ከተጠረጠሩበት ወንጀል በተጨማሪ በግድያ ወንጀል ጠርጥሬያቸዋለሁ ሲል አመልክቷል።

የምርመራ ቡድኑ ጉዳዩን ለፌደራሉ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ ችሎት ያመለከተ ሲሆን፥ ፍርድ ቤቱ ፖሊስ የጠረጠረበትን የግድያ ወንጀል ዝርዝር እና የምርመራ ሂደቱን ለችሎቱ እንዲያቀርብ ለህዳር 20 ቀን 2008 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ይዟል።

ከፖሊስ ባገኘነው መረጃ መሰረት መምህር ግርማ ወንድሙ እስከ ህዳር 20 2008 ዓ.ም ድረስ በእስር የሚቆዩ ይሆናል።

 

 

The post ዘ-ሐበሻ ኖቬምበር 5 ቀድማ በዘገበችው መሰረት ፖሊስ ዛሬ ለፍርድ ቤት መምህር ግርማን በግድያ ወንጀል እጠረጥራቸዋለሁ አለ appeared first on Zehabesha Amharic.

አዲስ ገጽ መጽሄት: የመጀመሪያ ዕትም ቅዳሜ ህዳር 12, 2008 ዓ.ም – PDF


ከመጠምጠም መማር ይቅደም |መስፍን ወልደ ማርያም [ፕሮፌሰር]

$
0
0

mesfin
ኅዳር 2008

በፌስቡክ የምንሰባሰበው ለመወያየት፣ አንዱ ከሌላው እንዲማር፣ መረጃዎችን በነጻነት እንድንለዋወጥ፣ ይህንን ሁሉ በማድረግ ራሳችንን ለማሻሻል፣ የእኛ መሻሻል እየተራባና እየተባዛ የአገርና የሕዝብ መሻሻል እንዲሆን፣ ከተቻለንም ከአገራችንና ከሕዝባችን አልፈን የምንታይ የዓለም አካል እንድንሆን መስሎኝ ነበር፤ ሳየው በዚያ መንገድ ላይ ያለንና ፌስቡክን ለበጎ ዓላማ እየተጠቀምንበት ያለን አይመስለኝም፤ ስለዚህ ወይ መታረም፣ አለዚያም በፌስቢክ ጊዜ ማጥፋቱን መተው ምርጫ ሊሆንብን ነው፡፡

ምናልባት 99.99% በእኔ ሰፈር ያሉ የፌስቡክ ተሳታፊዎች ወደፌስቡክ የሚገቡት ለመናገር ነው፤ መናገር የህልውናቸው ምስክር ወይም ማረጋገጫ አድርገው የሚወስዱት ጥቂት አይደሉም፤ ካልተናገሩ የሌሉ ይመስላቸዋል፤ ዋናው ነገር መናገር ይሆንና የሚናገሩት ነገር ወይም ጉዳይ ሌላው ቀድሞ ከተናገረው ጋር የሚያያዝ (የሚቃወመው ወይም የሚደግፈው) ሳይሆን ፈጽሞ ወደተለየ ጉዳይ ውስጥ ገብቶ አዲስ ርእስ መክፈት የተለመደ ነው፤ የአብዛኛው ፍላጎት ማስተማር ወይም ማሳወቅ ነው፤ ማስተማር ወይም ማሳወቅ ቀላል ነው፤ መናገር የሚችል ወይም ፊደሉን አውቆ መጻፍ የሚችል ማስተማር ይችላል፡፡

የትምህርት ቤት ጓደኛዬ በጃንሆይ ዘመን ትልቅ ሚኒስትር ነበር፤ በደርግ ዘመን ለብዙ ዓመታት ታስሮ ሲወጣ ሥራ አልነበረውም፤ ችሎታውን ስለማውቅ በዩኒቨርሲቲ እንዲያስተምር አመቻቸሁለትና ማስተማር ጀመረ፤ ከጥቂት ወራት በኋላ ስንገናኝ ‹‹እኔ ማስተማር ቀላልና እረፍት የሞላበት ሥራ ይመስለኝ ነበር፤ ለካ አንቅልፍ የሚያሳጣ ነው! እዝናናለሁ ባልሁ ቁጥር አንድ ክፍል ሙሉ ተማሪዎች ተሰብስበው ዓይኖቻቸውን እያቁለጨለጩ ምን እንደማስተምራቸው ሲጠብቁ ይታዩኛል! እረፍት ይነሡኛል!›› አለኝ፤ ከአንድ ዓመት በኋላ ማስተማሩን ተወ፤ ኅሊና ላለው ሰው ማስተማር ቀልድ አይደለም፤ ያደክማል፤ ለማስተማር መማር ያስፈልጋል፤ ለማሳወቅ ማወቅ ያስፈልጋል፤ ከመማር ይልቅ ማስተማር፣ ለማወቅ ከመጣር ይልቅ ለማሳወቅ መጣር የሚቀልለው ሰው የእውቀት ሰው አይደለም፤ ሌላ ሥራ ቢመርጥ ይሻለዋል፡፡

ሳያውቁ ለማሳወቅ አደባባይ መውጣት ከችኮላ ወይም ከስንፍና፣ ከትዕቢት ወይም ከግዴለሽነት የሚመጣ ነገር ይመስለኛል፤ ውሎ አድሮ ይጎዳል እንጂ አይጠቅምም፤ በአደባባይ መናገር ወይም መጻፍ የመጨረሻው መጋለጥ ነው፤ በአደባባይ መናገርና መጻፍ በሕዝብ ፊት መጋለጥ መሆኑን ብዙ ሰዎች አያውቁም፤ በአንጻሩ ደግሞ ብዙ ሰዎች ይህንን መጋለጥ ፈርተውትና ሸሽተውት የሚርቁት አሉ፤ መጋለጥን ፈርተው ዓይኖቻቸውን ዘግተው፣ ጆሮዎቻቸውን ደፍነው፣ አፋቸውን ለምግብና ለመጠጥ በቀር የማይጠቀሙበት፣ ዝምታ ወርቅ ነው እያሉ ወርቅ የሚሸምቱበት ብዙ ናቸው፤ ከሕዝብ ጋር እየተጓዙ፣ በሕዝብ መሀል እየኖሩ የሕዝብ ጉዳይ (ፖሊቲካ) አይመለከተንም የሚሉ የማሰብ ችሎታቸውን ህልውና ይጠራጠሩ፤ የማሰብ ችሎታ ከሌለ የማወቅ አምሮት ወይም ምኞት የሚኖር አይመስለኝም፤ የማወቅ አምሮት በሌለበት የማሳወቅ አምሮት ጎልቶ ሲወጣና ሲደናበር ማየት በጣም የተለመደ እየሆነ ነው፤ ፌስቡክ የሚባለው መድረክ የመደናበሪያ መድረክ እየሆነ ነው፡፡

የማሰብ ችሎታው የሌላቸው ሰዎች ከሁለት አንዱን መንገድ በመምረጥ፣ ወይም በሁለቱም መንገዶች በመጠቀም ይሳተፋሉ፡– የማያውቁትን ለማሳወቅ በመሞከርና በዘለፋ! የማያውቁትን ለማሳወቅ መሞከርና ዘለፋ የባሕርይ ግንኙነት አላቸው፤ አሁን እዚያ ውስጥ አንገባም፤ በተለያዩ መስኮች፣ በተለያዩ ጉዳዮች፣ በተለያዩ የእውቀት ጥበቦች በሚያሰራጩት ፍንጥቅጣቂ በአእምሮና በመንፈስ ለመበልጸግ በመጣር ፈንታ በአጉል ትዕቢትና ፉክክር፣ በማይጠቅም ዘለፋና ማስፈራራት የፌስቡክን መድረክ ማበላሸትና ማርከስ ወደኋላ ይጎትተናል እንጂ ወደፊት አያራምደንም፡፡

መሠረታዊ የማሰብ መነሳችን ሳንገነዘብ የማሰብ ትርምስምስ ውስጥ እንገባና መውጣት ያቅተናል፤ ለምሳሌ በእውቀትና በእውነት መሀከል ያለውን ልዩነት ሳንገነዘብ እምነትን ስንሞግት የራሳችንንም ሆነ የሌላውን ጊዜ እናጠፋለን፤ እውቀትን በሙግት ለማጣራት ሲመጡብን ደግሞ ቶሎ ወደእምነት እንዞራለን፤ አጉል መሽከርከር ውስጥ እንገባለን፤

እንዲያው በሆነ ባልሆነው፣ ባወቅነውም ሆነ ባላወቅነው የመጣልንን ሁሉ መዘርገፍ አዋቂ አያሰኝም፤ ጎበዝ አያሰኝም፤ ብልህ አያሰኝም፤ ግን ባለጌ ያሰኛል፤ ባለጌ ነጻነትን አያውቅም፤ ለባለጌ ስድነት ነጻነት ይመስለዋል፤ ነጻነት ባለቤቱ ያጠረው ገደብ ወይም ወሰን አለው፡፡

The post ከመጠምጠም መማር ይቅደም | መስፍን ወልደ ማርያም [ፕሮፌሰር] appeared first on Zehabesha Amharic.

“ወይ እነሱ ወይ እኔ ኢትዮጵያዊ አይደለንም”|በ4 ፖሊሶች የተደበደበው ሰው |ከያሬድ ሹመቴ

$
0
0

Yared

ካዛንቺስ ቶታት ፊትለፊት ጫጫ ኮርነር የተባለ ቤት በር ላይ የፒያሳ ታክሲ ለመያዝ ከምሽቱ 3:30 ገደማ በርካታ ሰዋች መሀል ቆሜያለሁ። 4 ፖሊሶች ደግሞ አለፍ ብለው ቆመዋል።

እድሜው ወደ 30ዋቹ መጨረሻ የሚሆነው አንድ ሰው በፌስታል የተቋጠረ ነገር ይዞ አቀርቅሮ ይጓዛል። ፖሊሶቹ አጠገብ ሲደርስ በመሀላቸው አቋረጠ። ከመሀላቸው ልጅ እግር የሆነው ፖሊስ ሰውየውን ጎትቶ ወደ ኋላ መለሰው።
“አቤት?” አላቸው ሰውየው።
“ለምንድነው በመሀላችን ያቋረጥከው?” አለው።
“አላየኋችሁም ይቅርታ”
“እንዴት አላየኋችሁም ትላለህ” አለው ሌላው
“ምን አጠፋው” ብሎ መለሰ
“ፖሊሶች እኮ ነን” አለው አንዱ
“ፖሊስ ማለት ህዝብ ነው” አለ ቆፍጠን ብሎ
“አንተማ ሌላ ተልዕኮ አለህ” ልጅ እግሩ ተናገረ።
“በስህተት በመሀላችሁ በማለፌ ነው ተልዕኮ ያለኝ?”

ታክሲ ለመሳፈር የተሰበሰበው ሰው ከንፈሩን እየመጠጠ ፖሊሶቹን በትዝብት ሲመለከት አንደኛው ፖሊስ “በቃ ና” ብሎ ወደፊት ጎትቶ ሲወስደው ሁሉም ተከተሉት።

ከፊት 2 ከኋላ 2 ሆነው ሰውየውን ይዘውት ሲሄዱ ታክሲ ተራው ላይ መቅረት አላስቻለኝም። ተከተልኳቸው። ከፊት ያሉት ሁለቱ ፖሊሶች እንደ ጓደኛ እያወሩት ይሄዳሉ። ወደ ፈንድቃ ባህል ምሽት ጋር ከመታጠፋቸው በፊት አንድ የብረት ፍርግርግ አጥር ያለው ጊቢ በር ከፍተው ገቡ። ኮምዩኒቲ ፖሊሲንግ የሚባል ቢሯቸው ነው።

የቢሮውን በር ከፍተው ሶስቱ ፖሊሶች ወደ ውስጥ ይዘውት ሲገቡ አንደኛው በረንዳው ላይ ቆሞ አካባቢውን ይቃኛል። እኔም እንዳያየኝ ካንትራት ታክሲ አስቁሜ ዋጋ መደራደር ጀመርኩ። ፖሊሱ ሰው አለማየቱን አረጋግጦ ወደ ውስጥ ሲገባ፥ ታክሲውን ይቅርታ ብዬው ወደ አጥሩ ተጠጋሁ።

የጊቢው አጥር እና ቢሮው ብዙም ርቀት የሌለው በመሆኑ በድንብ ይታያል። የበረንዳው መብራት እንደበራ ሲሆን ከፍተው የገቡትን ቢሮ መብራት አላበሩትም። ጨለማው ክፍል ውስጥ ሰውየው በመስኮቱ በኩል ከውጭ በሚገባው ብርሀን ይታየኛል።

ከመቅጽበት በሩ ተከፍቶ አንደኛው ፖሊስ ወደ ውጭ ወጣ። በረንዳው ላይ ቆሞ አላፊ አግዳሚውን መቃኘት ሲጀምር እኔም ታክሲ ጠባቂ መስዬ ቆምኩ። የሰውየውን ጩኸት ሰማሁት። የዱላ ድምጽ እና የሰውየው ጩኸት መንገደውኛውን ፊቱን ቢያስዞረውም ፖሊሱ አይኑ ፈጦ ሁሉንም ሰው ያይ ስለነበር ደፍሮ የቆመ የለም።

ጨለማ ቤት ውስጥ ለሚቀጠቀጠው ምስኪን ሰው አንጀቴ አረረ። ማድረግ የምችለው ነገር ምን እንደሆነ ጠፋኝ። የሰውየውም ድምጽ እና የዱላ ውርጂብኝ እየበረታ ሲሄድ አልቻልኩም። በፍጥነት ወደ 6ተኛ ፖሊስ ጣቢያ ሮጥኩ። የቂርቆስ ክፍለ ከተማ ዋና ፖሊስ መምሪያ (6ተኛ) አሁን ካለሁበት ብዙም ርቀት የሌለው በመሆኑ በፍጥነት ደረስኩ።

ጨለማ የወረሰው ግቢ ውስጥ ተረኛ ጥበቃ ፖሊሶች አግኝቼ አዛዦች ካሉ ብዬ ጠየቅኩ። “ማንም የለም ለኛ ንገረን” አሉኝ “አይ ሀላፊ ነው የምፈልገው” አልኳቸው። ሀላፊዎች የሉም ግን የመረጃ ክፍል ሄደህ ማነጋገር ትችላለህ አሉኝና ቢሮውን አመላከቱኝ።

ጨለማውን ኮሪደር አልፌ አንደኛ ፎቅ ላይ ወደሚገኘው መረጃ ክፍል ደረስኩ። አንድ ፖሊስ ብቻውን በርካታ የራዲዮ መገናኛ የድምጽ መሳሪያዎች ፊቱ ተደርድረው አንድ መዝገብ ላይ የሆነ ነገር እየፃፈ አገኘሁት።
“አስቸኳይ ጥቆማ ለመስጠት ነው” አልኩት።
“ምን ልታዘዝ” አለኝ። ፖሊሱ በጣም ትሁት ነው። የሆነውን በሙሉ ነገርኩት። ተናደደ።

በሬዲዮው መገናኛ የተለያዩ ኮዶችን እየጠራ የፖሊሶቹን ማንነት ለማጣራት ሞከረ። ተረኛ የጣቢያ አዛዡን ሞባይል ስልክ ቁጥር ጠይቆ ደወለ።
“ሀሎ … የት ነው ያለኸው?… 26 ያሉት ለምንድነው ሰው የሚደበድቡት?… ሰዋች በአካል መጥተው አባሎች ሰው እየደበደቡ ነው ብለው እየተናገሩ ነው። ጠቋሚ ሰዋቹ ‘በመሀላችን ለምን አለፍክ ብለው ነው የሚደበድቡት’ ነው የሚሉኝ…ፈጥነህ ድረስ…ቦታው ላይ ሂድ። ሰውየው ካለ ወደ ቤቱ የሚሄድበትን ወይም ወደ ህግ የሚሄድበት ነገር አድርግ። ህግ ከጣሰም በህግ ነው መቀጣት ያለበት እንጂ እንዴት በዱላ ይቀጣል?… እንደሰው አያስቡም እንዴ? ለምን አትነግሯቸውም? ሰው ለምን በመሀል አለፍክ ተብሎ ይደበደባል?…

…በባህላችን በሰው መሀል እንደማይታለፍ አስተምረኸው ታልፋለህ እንጂ ሰውን በዱላ ነው እንዴ የምታስተምረው?… እኔ ጋር ነው ያሉት የጠቆሙኝ ሰዋች… ምን?…ለምንድነው ወዳንተ ጋር የምልካቸው?… ወዳንተ ልኬ ደግሞ ልታስደበድባቸው ነው? ቶሎ ሂድና ያለውን ውጤት እኔ ጋር መጥተህ ንገረኝ።” ስልኩን ዘጋውና አመስግኖ አሰናበተኝ።

የሰውየው ነገር መጨረሻ አሳስቦኛል። እንደገና በሩጫ ትቼው ወደ ሄድኩት የኮምዩኒቲ ፖሊሲን ቢሮ አቅጣጫ ሄድኩኝ። መታጠፊያው አካባቢ ስደርስ ይህ ሰው እያነከሰ እና እየተንፏቀቀ ወደ እኔ አቅጣጫ ሲመጣ አየሁት። ያለቅሳል” ወይኔ” እያለ ግንባሩን ይደበድባል። “አይዞህ” አልኩት። “እባክህ ደግፈኝና 6ተኛ ፖሊስ ጣቢያ አድርሰኝ” አለኝ። የሆነውን በሙሉ እንዳየሁ ነገርኩትና ደግፌው ወደ ጣቢያው በድጋሚ ሄድኩ።

ፖሊስ ጣቢያው ጊቢ ውስጥ እንደገባን ሰውየው የቢሮው በረንዳ ላይ ተቀመጦ ለቅሶ እና የህመም ሲቃውን ቀጠለ። እኔን ያስተናገደኝ ፖሊስ እና የደወለለት ፖሊስ ተከታትለው መጡ። የሰውየውን ስም ጠየቁት “ዘላለም” አለ እያለቀሰ።

ዘላለም ብሶቱን በእንባ እና በለቅሶ መናገር ጀመረ።” “እኔ እኮ የተከተልኳቸው የናንተን ልብስ ስለለበሱ ነው። የፖሊስ ልብስ ባይለብሱ ኖሮ ጨለማ ክፍል ውስጥ ተከትያቸው እገባ ነበር? ህግ ቦታ እየወሰዱኝ ነው ብዬ ነው አምኜ የተከተልኳቸው። ምን አደረግኳቸው? ምን በደልኳቸው? አያውቁኝ! አላስቀይምኳቸው። ምን በድዬ ነው ምን አጠፋሁ ባልኩ የሚሰባብሩኝ?” እንባውን እየዘረገፈ ሲቃ እየተናነቀው ሲናገር ሀይለኛ ቁጣ እና ሀዘን ሆዴ ውስጥ ዘልቆ ገብቶ ጉሮሮዬን ሳግ ተናነቀኝ።

“ምን አድርጌ ነው። ለልጄ ልብስ እና ጫማ ገዝቼላት እንቅልፏን ሳትተኛ ልድረስ ብዬ ስሮጥ ጠልፈው ይቀጥቅጡኝ?!። እግዚአብሔር ፍርድ ይሰጣል እኔ ምንም አልልም እንባዬን እሱ ያብሰዋል። ምንም መናገር አልችልም ሌላ።”

ፖሊሶቹ የተመታውን እንዲያሳያቸው ባትሪ ወደ እግሩ አበሩ። ግራ እግሩ ክፉኛ አብጧል። እንባው እንደጎርፍ እየወረደ ለቅሶውን ቀጥሎ እያነከሰ ከተቀመጠበት ተነሳ። ፖሊሶቹ ነገ መጥተህ ክስ መስርት አሉት።

“እኔ ክሴ ለእግዜር ነው። እሱ ፍርድ ይስጥ። ብቻ ወይ እነሱ ወይ እኔ ኢትዮጵያዊ አይደለንም። አንዳችን ሀገር ክደናል። አይ ኢትዮጵያ! የፖሊስ ልብስ ለብሰዋል ብዬ ተከትዬ ስደበደብ እውነት ሀገር አለኝ እላለሁ? ነገም አልመጣም እናንተ ከሰማችሁኝ ይበቃኛል። ምን ፍርድ አገኛለሁ ብዬ ነው?” እንባውን እየጠራረገ ወደ ቤቱ ለመሄድ እያነከሰ መራመድ ጀመረ። ፖሊሶቹ ስልኩን ተቀበሉት። በነጋታው እንዲመጣ ቢለምኑትም ምንም ፍትህ ተስፋ እንደማያረግ ነግሯቸው እንባውን እያዘራ መሄድ ጀመረ። ከፖሊሶቹ ጋር ተሰናብቼ ደግፌው አብረን መሄድ ጀመርን።

ግማሽ መንገድ ሸኘሁት። “ወይ እነሱ ወይ እኔ ኢትዮጵያዊ አይደለንም” የሚለውን ቃል እየደጋገመ እንባውን እያፈሰሰ ወደ ቤቱ በእየተሳበ ሄደ።
፡።።።
ሀቀኛ ፖሊሶች ካላችሁ ልብሳችሁን አስከብሩ።
።።።።

እነዚህን 4 ፖሊሶች በህግ ተጠያቂ ይሆኑ ዘንድ ይህንን መልዕክት Share በማድረግ ሀላፊነትዎን ይወጡ።
።።።።
ዘላለምን ግን ቸር አምላክ ምህረቱን ያውርድለት።

The post “ወይ እነሱ ወይ እኔ ኢትዮጵያዊ አይደለንም” | በ4 ፖሊሶች የተደበደበው ሰው | ከያሬድ ሹመቴ appeared first on Zehabesha Amharic.

የሕወሓት አስተዳደር አዲስ አበባን “እናሰፋለን”በሚል ሰበብ የሚሰራው ሸፍጥ ተጋለጠ (ምስጢራዊውን ደብዳቤው ይዘናል)

$
0
0

(ዘ-ሐበሻ) በኦሮሚያ ክልል የተለያዩ ከተሞች ከባለፈው ዓመት ጀምሮ ሕዝቡ ሕወሓት የሚመራው መንግስት ያዘጋጀው የአዲስ አበባ ማስተር ፕላንን በመቃወም አደባባይ በመውጣቱ ለበርካቶች ሕይወት መጥፋት እና ለበርካቶች መቁሰል ምክንያት እንደነበር ይታወሳል:: እነዚህ ለተቃውሞ አደባባይ የወጡ የሃገራችን ፍሬዎች ምክንያታቸው በአዲስ አበባን የማስፋፋት ምክንያት ምስኪን ገበሬዎችን በማፈናቀል መሬታቸውን ለባለሃብቶች ለመሸጥ ነው የሚል ነው:: ሕወሓት የሚመራው መንግስት “በልማት” ስም የተለያዩ የሃገራችንን መሬቶች ገበሬዎቹን በማሰናበት ለውጭ ባለሃብቶች በመሸጥ ይታወቃልና ወትሮም እነዚሁ በኦሮሚያ ክልል ያሉ ሕዝቦች አደባባይ ወጥተው ይህን በአዲስ አበባ ዙሪያ ያሉ ገበሬዎችን ያፈናቅላል ያሉትን አዲሱን ማስተር ፕላን ቢቃወሙ አይገርምም::

ዛሬ የተለቀቀው ምስጢራዊ ደብዳቤ በአዲስ አበባን የማስፋፋት ስም በሕወሓት መንግስት የሚደረገውን ጥልቅ ሴራ ያጋለጠ ነው:: ምስጢራዊው ደብዳቤ እንደሚያሳየው ‘ሆዜ ሂማንተሪያን ፋውንዴሽን” የተሰኘ ድርጅት የመለስ ዜናዊን መንደር በሰበታ አዋስ ወረዳ ያቀረበውን ጥያቄ ወረዳው መቀበሉን ያረጋገጠበት ነው:: ደብዳቤው እንደሚለው ለመለስ ዜናዊ መንደር ግንባታ ለሆዜ ፋውንዴሽን አንድ ሺህ ሁለት መቶ ሄክታር ወረዳው እንዲያዘጋጅ መጠየቁን እና ይህንንም ማዘጋጀቱን ነው::

እንግዲህ አዲስ አበባን እናስፋፋለን የሚሉት ምስኪን ገበሬዎቹን አፈናቅሎ ምን ለመፍጠር እንደሆነ ከዚህ በታች ከቀረበው ደብዳቤ ይረዱና አስተያይትዎን ያስቀምጡ::
addis Ababa

The post የሕወሓት አስተዳደር አዲስ አበባን “እናሰፋለን” በሚል ሰበብ የሚሰራው ሸፍጥ ተጋለጠ (ምስጢራዊውን ደብዳቤው ይዘናል) appeared first on Zehabesha Amharic.

የኢትዮጵያ የረሃብ አዙሪት ችግር፣ ሳይንሳዊና ፖለቲካዊ ጠቋሚ መፍትሄዎቹ |ዶ/ር ዘላለም ተክሉ

$
0
0

 

11/28/2015

በሰሞኑ በኢትዮጵያ ለረሃብ የተጋለጡትን ወደ 15 ሚሊዮን የሚጠጉ ወገኖቻችን አስመልክቶ በሃገር ውስጥና ከሃገር ውጭ ባሉ ኢትዮጵያውያን መካከል ከፍተኛ የሃሳብ ልውውጥና ክርክር እየተደረገ ይገኛል:: አገሪቱን እያስተዳደረ ያለው “መንግስት” ችግሩ በቁጥጥሩ ስር እንደሆነና፣ የምግብ እጥረቱን በውጭ ግዥ ለማሟላት በከፍተኛ ደረጃ እየተንቀሳቀሰ እንዳል ይገልጻል:: በሌላ ወገን የሚከራከሩ ወገኖች ደግሞ ችግሩ “መንግስት” እንደሚለው ቀላል እንዳልሆነ፣ ሁኔታዎችም ከቁጥጥሩ ውጭ እየወጡ እንደሆነና መላው ህዝባችን( የሃገር ውስጥና ውጭ ያለው ሁሉ)ተባብሮ ካልተንቀሳቀሰ ረሃቡ ለብዙ ወገኖቻችን እልቂት ምክንያት እንደሚሆን ስጋታቸውን እየገለጹና ዕርዳት በማሰባሰብ ላይ እንደተጣደፉ እንደሆነ ይስተዋላል::

File Photo

File Photo

የረሃቡን ምክንያት በተመለከተ የገዢው “መንግስት” ባላስልጣናት ችግሩ “ኤልኒኖ” በተባለ የተፈጥሮ መዛባት ምክንያት የመጣ መሆኑን፣ ነገር ግን ሃገሪቱ ቀደም ባሉት አመታት ባስመዘገበችው የኢኮኖሚ ልማት በተለይም በከፍተኛ የግብርና እድገት ምክንያት እስከ 270 ሚሊዮን ኩንታል እህል በዓመት የማምረት አቅም በመፍጠሯ ችግሩን በሃገር ውስጥ ጥረት ብቻ መቋቋም እንደሚቻል በኩራት ሲናገሩ ይሰማል::

ይህን “የመንግስት” ተደገገሚ ምክንያት የሚቃወሙ ወገኖች ደግሞ በእውነት ላለፉት 10 አመታት የተፎከረለት ዕድገት ቢኖርና በየዓመቱም ከ 270 ሚሊዮን ኩንታል ማምረት የተቻለ ቢሆን ኖሮ 15 ሚሊዮን ይቅርና አንድም ሰው ሊራብ እንደማይገባው ይከረከራሉ:: የእስከሚሰለች የሚነገረን የ 10 ዓመቱ ዕደገትና የግብርና ምርቱ ብዛት እንዴት  ለገበሬው ትርፍ ጥሪት አላጎናጸፈውም ብለው ይጠይቃሉ፣ ብዙ ሚሊዮነሮችን ያፈራው ዕድገት እንዴት በአንድ ክረምት ኤልኒኖ የሚጠቁ 15 ሚሊዮን ወገኖችን ሊየፈራ ቻለ ብለው ይሟገታሉ:: በዚህም የተነሳ  ብዙዎች ከዚህ ቀደም እንደሚሉት “የመንግስት ዕድገት” ከቁጥር ቅቀላ የማያልፍ “ የፕሮፖጋንዳ ዕድገት” እንደሆነ  አበክረው ያሳስባሉ::

እኔም በዚህ አጭር ጽሁፍ እውነት ዕድገት ቢኖር ኖሮ ቅንጣት ታክል እንኳን ረሃብ ሊኖር አይገባም የሚለውን መከራከሪያ በመደገፍ ሳይንሳዊ ንድፈ ሃሳብና ተሞክሮን በማጎዳኘት ሙግቱን ለማጣናከር እሞክራለሁ:: ለዚሁ ሙግት እንዲረዳኝ በመጀመሪያ “ድህነትና ረሃብን” በተመለከተ የኢኮኖሚክስ ኖቤል ተሸላሚ የሆነው ህንዳዊው ምሁር አማርቲ ሴን ፈጠራ ሥራ የሆነውን ንድፈ ዝርዝር ጥናት ተጠቅሜአለሁ::

የአማርቲ ሲን ንድፈ ሃሳብ የሚጀምረው የሰው ልጅ ለመኖር የሚያስፈልጉትን ነገሮች የማግኘት መብቱ ወይም በእንግሊዝኛ “ Entitlement” ተብሎ ከሚጠራው መነሻ ትርጓሜ ይሆናል:: የዚህ ትርጓሜ ቀጥተኛ እንግሊዝኛ ይዘቱም እንደሚከተለው ሲሆን:-

A person’s “entitlement set” is the full range of goods and services that he or she can acquire by converting his or her “endowments” (assets and resources, including labor power) through “exchange entitlement mappings” (Sen, 1981, Vol 96, No 3, pp 433-465).

የአማርኛ ግርድፍ ትርጉሙም ማንኛውም የሰው ልጅ ያለውን ጥሪት፣ ሃብትና ጉልበት ገበያ ወስዶ በመቀየር ለእለት ኑሮው አስፈላጊ የሆኑ ምርቶችና አገልግሎቶችን ማግኘት የመቻል መብት አለው ማለት ነው::

አማርቲ ሴን ይህን ጥቅል “endowment” ምግብን ከማግኘት ህጋዊ አቅም አንጻር በአራት ንዑስ ሃሳቦች ይከፍለዋል::

1) ምግብ ማምረት ከመቻል መብት አንጻር “production-based entitlement “

2) ምግብ መግዛት ከመቻል መብት አንጻር “trade-based entitlement”

3) ምግብ ለማግኘት ከመስራት መብት አንጻር “own-labor entitlement”

4)ምግብን ከሌሎች ወገኖች በዕርዳታ ከማግኘት አንጻር “inheritance and transfer entitlement”

በዚሁ መሰረት የሰው ልጅ ለህይወቱ የሚያስፈሉጉትን ቁሳቁሶች ከላይ ከተዘረዘሩት ንዑስ ህጋዊ መብቶችና ምንጮች ውስጥ የተወሳኑት ወይም አብዛኞቹ ካልተሟሉለት ለረሃብ ይጋለጣል ተብሎ ይታመናል::

አማርቲ ሴን ከላይ የተዘረዘረውን ንድፈ ሃሳብ በመጠቀም እ.ኤ.አ በ1943 በህንድ ቤንጋል፣ በ1973 በኢትዮጵያ ወሎና በ 1974 በባንግላዴሽ ተከስተው ከመቶ ሺህ እስከ ሚሊዮን ህዝብ ያለቀበትን የረሃብ ወቅቶች ገምግሞ የእልቂቱ ምክንያት የምግብ እጥረት ሳይሆን ከላይ የተዘረዘሩት ምግብ የማግኛ አቅሞችና መብቶች entitlements ካለሟሟለት እንደሆነ  አራጋግጧል::በተለይም በኢትዮጵያ በወሎ ክፍለሃገር እ.ኤ.አ ከ 1973 -1974 ለተከሰተው ረሃብ መነሻ ምክንያት ለሁለት ዓመታት የቆየው የዝናብ እጥረት ቢሆንም እንኳን እስከ  200,000 የሚገመት ህዝብ በረሃብ የረገፉት በተለይ ከራያና ቆቦ፣ የጁና አምባሰል አውራጃዎች ምግብ በበቂ ሁኔታ ማምረትና ከገበያ የመግዛት መብትና አቅም ቀድሞውኑም ያጡ ምስኪን  ድሆች እንደነበሩ ጥናቱ አረጋግጡዋል:: የዝናብ እጥረቱ በወሎ ክፍለ ሃገር ባጠቃላይ የምግብ እጥረት ቢፈጥርም እንኩዋን በሌሎቹ የወሎ አውራጃዎችና፣ ከተሞች የሚገኘው አብዘኛው ህዝብ ለእለት የሚያስፈልገውን የካሎሪ መጠን ሊያሟላ የሚችል ምግብ ከሌሎች ክፍለ ሃገሮች በማስመጣት ችግሩን አልፏል:: እዲያውም  በረሃቡ ወቅት ከወሎ ወደ አዲስ አበባና አስመራ የተጫነ እህል እንደነበር የሚያረጋግጥ መረጃ እንደነበር ተረጋግጡዋል:: በዛን ጊዜ በወሎ ክፍለሃገር ይተዳደሩ የነበሩት የአፋር ዘላን ወገኖች እንኳን ምግብ ማግኘት በመቻላቸው አንድም ግለሰብ ለረሃብ እንዳልተጋለጠ ተመዝግቧል::

ከላይ የተገለጹት መረጃዎች ሲመረመሩ ለረሃቡና እልቂቱ ምክንያት የምግብ እጥረቱ ነው ብሎ መደምደም እንደማይቻል መያስረዷል:: እጥረቱ ቢኖርም እንኩዋን ወደ ወሎ  ክፍለ ሃገር የሚወጣና የሚገባ የምግብ ዝውውር ነበርና:: ዋናው ችግር በምግብ ዝውውሩ ለመሳተፍ የማይችሉ የህብረተሳብ ክፍሎች ቀድሞውኑም መኖራቸው ሲሆን ይህም ሊሆን የቻለው ምግብ የማምረት፣ ገዝቶ ራሳቸውን የመመገብ መብታቸውና አቅማቸው በመሟጠጡ እንደሆነ ለማወቅ ይቻላል::

በነዛ ሶስት አውራጃዎች በረሃብ እየተጠቁ ወገኖች ምግብ በቶሎ አድርሶም ከሞትለመታደግ ያልተቻለው የትራንስፖርት ተቋማት በወሎ ክፍለ ሃገር በበቂ ሁኔታ አለመኖር ነው የሚልም መከራከሪያ በወቅቱ ቀርቦ ነበር:: ነገረ ግን ለእነዚህ አውራጃዎች የሚሚያገለግሉ የመርጂያ ጣቢያዎቾ ባብዛኛው ከአዲስ አበባ አስመራ በሚያደርሰው ዋና አውራ ጎዳና ላይ የተቋቋሙ በመሆናቸው ይህ ምክንያት ውሃ እምደማይቋጥና ለእልቂቱ ዋነኛ ምክንያት ከ entitlement እጦት ውጭ እንዳልነበረ የበለጠ ማራጋጋጫ ሆኖ ተመዝግቧል::

ከላይ የተገለጠውን ትንተና መሰረት በማድረግ እኔም  በሃይለስላሴና በደርግ ዘመናት ብቻ ሳይሆን አሁን ባለው “መንግስታችን” አገዛዝ ዘመን እየተደጋገመ ያለው የረሃብ አዙሪት ምስኪኑ የገጠሩ ህዝባችን በገጠመው ምግብ የማምረት፣ ጥሪት አፍርቶ ራሱንና ቤተሰቡን የመመገብ፣ ችግር ሲገጥመው በወቅቱ የምግብ ዕርዳታ የማግኛት መብትና አቅም በመጣቱ ብቻ ነው እላለሁ::እስቲ በወያኔ ዘመን ያለውን የገበሬውን አቅምና መብት (entitlement) እንመልከት:

1 ምግብ ማምረት ከመቻል መብት አንጻር

90 በመቶ የሚሆነው ገበሬ ምግብ የሚያመርተው ከሁለት ሄክታር ባነሰ መሬት ላይ ሲሆን ከዛሬ 60-70 ዓመታት በፊት በሚጠቀምበት የሞፈርና ቀንበር ቴክኖሎጂ ሳይወጣ እንዴት አድርጎ ራሱንና ቤተሰቡን ሊመግብ የሚችል እህል እንዴት ማምረት እንደሚችል መገመት በጣም ይቸግራል:: ያም አልበቃ ብሎ ማዳበሪያና ፀረ ተባይ መድሃኒት በብድር ወስዶ እንዲጠቀም ገበሬው በወያኔ ካድሬዎች እየተገደደ ይገኛል:: በሌላም በኩል ገበሬው ቤተሰቡ እየጨመረ ሲሄድና ለአቅማዳምና ለሥራ የደረሱ ልጆቹ ከዛችው ብጣቂ መሬት ላይ ድርሻቸውን እየወሰዱ ሲሄዱ የቤተሰቡ ምግብ የማምረት መብትና  አቅም እንዴት እየተገፈፈ እንደሚሄድ መረዳት ተፈላሳፊነት አይጠይቅም:: ሌላም ነገር አለ:: ገበሬው በቤቱ ዙሪያ ዛፍ ወይም ሌሎች ቋሚ ተክሎች ላይ መዋእለ ነዋይ ለማፍሰስ አይደፍርም፣ ምክንያቱም የመሬት ይዞታው የራሱ ሆኖ ለዓመታት  እደሚዘልቅ ምንም ዋስትና የለውም:: ባላፈፉት 10 ዓመታትም የያዘውን ብጣቂ መሬት እየተነጠቀ ለውጭና ለወያኔ ወጋኝ “ ልማታዊ” ሰፈፊ እርሻ አልሚዎች መሰጠቱ ብዙ ድሃ ገበሬዎች ምግብ የማምረት መብትና አቅም እንዳሳጣቸው በስፋት ይነገራል::

2 ምግብ መግዛት ከመቻል መብት አንጻር

በተበጣጠሰና የይዞታ ዋስትናው ባልተረጋገጠ መሬት እንዲያርስ መደረጉ፣ ኋላ ቀር ቴክኖሎጂና አለፍላጎቱ ማደበሪያ ገዝቶና ተበድሮ እንዲጠቀም መገደዱ፣ የሃገራችንን  አብዛኛው ገበሬ ምግብ የማምረት መብቱንና አቅሙ እንዲዳከም እንዳደረገው ከላይ መተንተኑ ይታወቀል:: ገበሬው ከሁለት ሄክታር ባነሰች ኩርማ መሪቱ ካመረታት ጥቂት ኩንታል እህል ውስጥ የተበደረውን ብድር እንዲከፍል ሲገደድ፣ በጎተራው የምትቀረው እህል እንዴት ተሟጣ እንደምትቀር ይታያችሁ:: በዚህ ሁኔታ የገበሬው ምርት የተሟጠጠ ከሆነ ለዓመት አይደለም ለወራት እንኳን ቤተሰቡን መመገብ አይችልም፣ ለረጅም ጊዜም የሚረዳ የምግብና ገንዘብ ጥሪት ሊይዝም አይችልም::   ሁኔታዎች እንደዚህ ባሉበት ሁኔታ የዝናብ እጥረቱ ከአንድ ወደ ሁለት ዓመታት ከተሸጋገረ፣ አብዛኛው ገበሬ የሚያመርተው ምርት አይኖርም:: ካለፉት ዓመታት ምርቱም ምንም ጥሪት ባለመያዙ ከትርፋማ አካባቢ በርካሽ ዋጋ እህል በገበያ ቢቀርብ እንኳን ገበሬው የመግዛት ዓቅም አይኖረውም::

አሁን ለረሃብ የተጋለጡት 15 ሚሊዮን ወገኖቻችን የዚሁ ምግብ የመግዛት መብትና አቅም መሟጠጥ ውጤት ናቸው:: ከ 6 – 7 ወራት በፊት መንግስትና ረጂ ድርጅቶች ለረሃብ ተጋለጡ ሲሏቸው የነበሩት ወገኖች ከ 2 እስከ 3  ሚሊዮን አይበልጡም ነበር:: የረሃብተኛው ቁጥር ወደ 15 ሚሊዮን ከፍ እያለ የመጣው የዝናብ እጥረቱ ሁለት የምርት ዘመናትን እየሸፈነ በመምጣቱና በዚህም ምክንያት በሚከሰተው የምርት እጥረት የመግዛት አቅማቸው እየተመናመነ የመጣባቸው ወገኖች ቁጥር እየጨመረ በመሄዱ ነው:: አያድርገውና  የዝናብ እጥረቱ ለተጨማሪ ክረምት ከቀጠለ፣ በመግዛት መብትና አቅም በመመናመን የሚራቡት ወገኖቻችን ብዛት ወደ 20 እና  25 ሚሊዮኖች ሊሸጋገር እንደሚችል  ስጋቶች እየታዩ ነው::

3ምግብን ከሌሎች ወገኖች በዕርዳታ ከማግኘት አንጻር

በምግብ እጥረት ወቅት በረሃብ የተጋለጡ ወገኖች ምግብ በአፋጣኝ እንዲያገኙ ስለሚደረግ ጥረት አማርቲ ሴን የህንድን የ 1966/67 እና የ የ ቻይና የ 1958-61 ረሃቦችን በምሳሌነት ተጠቅሟል:: ህንድ ከእንግሊዝ ቅኝ ግዛት ነጻ እስክትወጣ ድረስ ለተደጋጋሚ ረሃብና እልቂት ተጋልጣለች:: ከነጻነቷ በኋላ በ1966/67 የተከሰተው የቢሃር ረሃብ ግን በቁጥጥር ስር እንዲውል ተደርጓል:: ይህም ሊሆን የቻለው ህንድ የብዙሃን ፓርቲና ዲሞክራሲ ማስፈን ከቻለች በኋላ ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ ባህል መዳበር፣ የህዝብን ችግር ሊፈቱ የሚችሉ የፖለቲካ መሪዎች፣ አገር አስተዳዳሪዎችና የስራ አስኪያጆችን በዲሞክራሲያዊ መንገድ መምረጥና ሃላፊነታቸውን ባግባቡ መወጣት ካልቸሉ መሻር በመቻሉ፣ የምግብ እጥረት ሲከሰት በአፋጣኝ እርዳታ እንዲደርስ የሚዘግብና የመፍትሄ እርምጃዎችም በወቅቱ መወሰዳቸው የሚከታተል ነጻ ሚዲያ መፈጠች በመቻሉ ነበር::

ከ 1958-61 በቻይና የተከሰተው ረሃብ ግን ምንም ህዝብና የፖለቲካ ልሂቃንና ተቋማቶች ሳያውቁት ከ 16.5 እስከ 29.5 ሚሊዮን ህዝብ  እንዳለቁ ተዘግቧል:: ማኦ ዜዱንግና የቻይና ኮሚኒስት ፓርቲም ይህን ያህል ህዝብ እንዳያልቅ መከለከል ያልተቻለበት ምክንያት ምግብ የማምረትና የመግዘት መብቱና አቅሙ የተሟጠጠበት ህዝብ ዕርዳት በአፋጣኝ አለማግኘቱን የሚያጋልጡና የሚከታተሉ ነጻ ፕሬሶች አለመኖራቸው እንደሆነ ማመናቸውና ከዚያም በኋለ ብዙ ማስተካከየ እርምጃዎችን እንደወሰዱ ተዘግቧል::

በሃገራችን በኢትዮጵያም ለረሃብ የተጋለጡ ወገኖች ለሞት ሳይደርሱ የምግብ ዕርዳት አላማግኘት ችግር በሃይለስላሴ ፣በደርግ እና በወያኔ ዘመንም ተመሳሳይ ነው:: በሁሉም ጊዜያት የገዢው ወገኖች ከፍተኛ የሆነ  የልደትና የፓርቲ ድግሶችን እያደረጉ ባሉበት ወቅት የተራቡ ወገኖች ወደከተማ እንዳይሰደዱ፣ በቲሌቪዝንና በሬዲዮ እንዳይሰሙ እዲሁም የተራቡት ወገኖች ብዛት ቁጥሮችን ማሳነስ የተለመዱ የመሸፋፈኛ እርምጃዎች ናቸው::የወያኔ መንግስት ማንኛውንም የሃገር ውስጥና የውጭ ጋዜጠኞች ባሁኑ ሰዓት እየተባባሰ ስለመጣው ረሃብ ምንም ነገር እንዳይዘግብ የከለከለ ሲሆን “በወቅቱ ረሃብ ልጄ ሞተብኝ” ብለ ለ BBC ዘጋቢ ሃሳቧን የሰጠችውን የወሎ  ረሃብተኛ መልሳ እንድታስተበብል መደረጓ ተሰምቷል:: ይኽው “ መንግስት” ባንድ በኩል ችግሩን በቁጥጥሩ ስር እንዳደረገው፣ ያለማንም ዕርዳታ ምግብ ከውጭ ገዝቶ ለችግረኞቹ እንደሚደርስላቸው ሲፎክር፣ በሌላ በኩል ደግሞ የዓለማቀፉ ህብረተሰብ ችግሩን ለመፍታት አልተንቀሳቀሰ በማለት ወቀሳ እየቀረበ ይገኛል:: በዚህ ግርግር መሃል ግን የተራበው ወገናችን ምግብ ባፋጣኝ ሊደርስላቸው እንዳልቻለና በዚያውም ምክንያት ብዙ ወገን በሞት አፈፍ ላይ እንደደረሱ እየተዘገብ ይገኛል::

ባጠቃላይ “መንግስታችን” እንደሚፎክረው በሁለት ዲጂት እያደገ ባለበት ኢኮኖሚና ከድህነት ወለል በታች የሚኖሩት ወገኖቻች መጠን ከ 44% ወደ 31% ዝቅ ማለቱ በተለፈፈበት ሁኔታ፣ በአስር ሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ምግብ የማምረት፣ የመግዛትና ዕርዳታ የማግኘት መብትና አቅም ያጡ ገበሬዎች መከሰታቸው ሲታይ  የወያኔ  ፖለቲካ “ሁሉም ዜሮ ዜሮ” የሆነ “ፕሮፓጋንዳ” ብቻ እንደሆነ ማረጋገጥ ይቻላል::

የተራቡት ወገኖቻችንን ከሞት ለመታደግ ዕርዳታ ማሰባሰብና እንዲደርሳቸው ማድረግ ታላቅ የዜግነት ግዴታችን ነው:: ነገር ግን በየ 5 እና  10  ዓመታቱ የሚከሰተውን የረሃብ አዙሪት በዘላቂነት ከመፍታት ረገድ የሚኖረው አስተዋጽኦ ግን በጣም አናሳ ነው:: የዚህ የረሃብ አዙሪት ዘላቂው መፍትሄ  የገበሬውን ምግብ የማምረት፣ ምግብ የመግዛትና በእህል ምርት እጥረት ጊዜ ባፋጣኝ ምግብ የሚያገኝበት መብትና አቅም እንዲገነባ ማድረግ ነው:: ለዚህ መሳከት ደግሞ ዲሞክረሲና ነጻ ገበያን ማዕከል ያደረጉ ህጎች፣ ፖሊሲዎችና እስትራቴዎጅን ተግባሪዊ ማድረግ ብቸኛ መንገድ ነው:: በኔ ግምት እነዚህ ህጎች፣ ፖሊሲዎችና እስትራቴዎጅ  አሁን እየገዛን ባለው “ መንግስታችን” ተግባሪያዊ እየሆኑ አይደሉም ይሆናሉ ብዬም በፍጹም አልጠብቅም:: ስለዚህ በየጊዜው እየተራቡ የሚሰቃዩትን ወገኖቻችንን በዘላቂነት ለመታደግ ከፈለግን፣ ያለውን ገዢ “መንግስት” በዲሞክራሲያዊ ስርዓት ለመለወጥ እየተደረገ ላለው ትግል የራሳችንን አስተዋጽዖ ማድረግ ግዴታች ነው ብዬ አምናለሁ፣ ጥሪም አስተላልፋለሁ::

በተረፈ ቸር ይግጠመን::

The post የኢትዮጵያ የረሃብ አዙሪት ችግር፣ ሳይንሳዊና ፖለቲካዊ ጠቋሚ መፍትሄዎቹ | ዶ/ር ዘላለም ተክሉ appeared first on Zehabesha Amharic.

አርቲስት ፍቃዱ ተ/ማርያም ፍ/ቤት ቀረበ

$
0
0
File Photo

File Photo

 አለማየሁ አንበሴ ለአዲስ አድማስ ጋዜጣ እንደዘገበው

አንጋፋው ተዋናይ አርቲስት ፍቃዱ ተ/ማርያም በሽርክና የሚያሳትመውን የመረጃና የስልክ አድራሻ ማውጫ ዳይሬክተሪ፤ አመሳስለው በማዘጋጀት ለገበያ አቅርበውብኛል ባላቸው አካላት ክስ መስርቷል “እንደ ልጄ የማየውን ሥራዬን ነው የወሰዱብኝ” ብሏል – አርቲስቱ፡፡
በአቃቤ ህግ የቀረበው የክስ መዝገብ እንደሚያስረዳው፤ ዌብ ፕላኔት አይቲ ሶሉሽን እና ስራ አስኪያጁ አቶ ዳንኤል ታፈሰ በ1999 የንግድ ፍቃድ የተሰጠው የአርቲስት ፍቃዱ ተ/ማርያም የኪነ ጥበብና የማስታወቂያ ስራዎች ድርጅት፣ “የኢትዮጵያ የመረጃ እና ግብይት ዳይሬክቶሪ” የተሰኘ የአድራሻና የመረጃ ዳይሬክትሪን የመረጃ ቅንብር (ዳታ ቤዝ) በማመሳሰል፣ “National Info and Business Directory” በሚል ርዕስ አዘጋጅቶ በ117 ሺህ ብር የማስታወቂያ ክፍያ በመሸጥ በተበዳይ ላይ ጉዳት አድርሰዋል::
ተከሳሹ የንግድ ፍቃድ ሳይኖራቸው ዳይሬክተሪውን አሳትመው ማሰራጨታቸውም በክሱ ተጠቅሷል፡፡ አቃቤ ህግ 7 የሰው ምስክሮችና የሰነድ ማስረጃዎችን ያቀረበ ሲሆን ባለፈው ማክሰኞ ሰባቱም ምስክሮች ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡
ከአቃቤ ህግ ምስክሮች አንዱ ሆነው የቀረቡትና በአርቲስት ፍቃዱ ተክለማርያም የኪነ ጥበብና ማስታወቂያ ድርጅት ውስጥ የ50 በመቶ ድርሻ ያላቸው ኢ/ር ብስራት ዳንኤል በሰጠው ቃል የዳይሬክተሪውን ሙሉ የመረጃ ቅንብር (ዳታ ቤዝ) እሳቸው እንዳዘጋጁት ጠቁመው፣ ተከሳሽ የመረጃ ቅንብራቸውን ሙሉ ለሙሉ በመገልበጥ ማሳተማቸውን ተናግረዋል፡፡ ድርጅቱ ከተመሰረተ ጀምሮ 4 ተከታታይ ህትመቶችን ማውጣቱን የገለፁት ምስክሩ፤ የተወሰደባቸው የመረጃ ቅንብር ለ2012/13 እ.ኤ.አ ያዘጋጁት ሲሆን ተከሳሹ ለ2014/15 በሚል ወቅታዊ አድርገው ማሳተማቸውን አስረድተዋል፡፡
ሐምሌ 20 ቀን 2006 ዓ.ም ህትመቱን ከቻይና ወደ ሀገር ውስጥ ያስገቡት ተከሳሹ፤ ነሐሴ 14 ቀን 2006 ዓ.ም ከጉምሩክ በማስወጣት፣ ማሰራጨት መጀመራቸውን ምስክሩ ጠቅሰው ለተለያዩ ድርጅቶች በአጠቃላይ በ117ሺ ብር አሰራጭተዋል ብለዋል፡፡ የተከሳሹ ዳይሬክተሪ በድርጅታቸው ከሚታተመው ዳይሬክተሪ ጋርም በስያሜ፣ ውስጥ ባሉ መረጃዎችና አቀማመጣቸው፣ በወረቀትና ቀለም አጠቃቀምና በማስታወቂያ አቀማመጥ እንደሚመሳሰሉ ተናግረዋል፡፡
ተከሳሹ፤ በአርቲስት ፍቃዱ ድርጅት ውስጥ የሽያጭ ሰራተኛ አስተባባሪ ሆነው ይሰሩ እንደነበር ያስታወሱት ምስክሩ፤ በ2002 ከድርጅቱ ከወጡ በኋላ ወረቀትና የወረቀት ውጤቶችን የማስገባት ፍቃድ እንጂ የማስታወቂያ ስራ ፍቃድ ሳይኖራቸው ነው ዳይሬክተሪውን ያሳተሙት ሲሉ ለፍ/ቤቱ አብራርተዋል፡፡ ተከሳሹ ጉዳዩ በፍ/ቤት ተይዞ ሳለም ሁለተኛ ህትመት ማሳተማቸውንም ምስክሩ ተናግረዋል፡፡
ሁለተኛ የአቃቤ ህግ ምስክር ሆኖ የቀረበው ራሱ አርቲስት ፍቃዱ ተክለማርያም ሲሆን፤ “ከቲያትር ስራ ጡረታ ከወጣሁ በኋላ መጦሪያዬ ይሆነኛል ያልኩትንና እንደ ልጄ የማየውን ስራዬን ነው ተከሳሽ የወሰዱብኝ” ብሏል፡፡ “ስምንት ዓመት የለፋንበትን ነው ገልብጠው ያሳተሙብን” ያለው ምስክሩ፤ ስራችን የመንግስት አካላት ተገቢ እውቅና የሰጡበት ነው ብሏል፡፡
ፍ/ቤቱ የአቃቤ ህግ ምስክሮችን በሙሉ ካደመጠ በኋላ ተከሳሽ እንዲከላከሉ በማለት ምስክሮችን ለመስማት ለጥር 3 ቀን 2008 ዓ.ም ቀጥሯል፡፡

The post አርቲስት ፍቃዱ ተ/ማርያም ፍ/ቤት ቀረበ appeared first on Zehabesha Amharic.

የሞጋቾች ድራማ ደራሲ ኃይሉ ጸጋዬ ከፕሮዲውሰሯ መቅደስ ጸጋዬ ጋር ስላላግባባቸው ጉዳይ ተናገረ

$
0
0

ባለፈው ሃሙስ ዘ-ሐበሻ ድረገጽ “ሞጋቾች ድራማ የዘገየበት ምክንያት ታወቀ” በሚል ዘገባ ካቀረበች በኋላ በኢትዮጵያ ቅዳሜ ዕለት ታትመው የወጡት ጋዜጦች እና መጽሔቶች ትኩረታቸውን በዚህ ድራማ ውዝግብ ዙሪያ አድርገዋል:: ከነዚህም ሚድያዎች መካከል አዲስ አድማስ ጋዜጣና ቁምነገር መጽሔቶች ይጠቀሳሉ:: ሁለቱም የመረጃ ምንጮች ሰፋ ያለ ዘገባ ያቀረቡ ሲሆን ልክ ዘ-ሐበሻ እንደዘገበችው ድራማው ካሁን በኋላ በሃይሉ ጸጋዬ ሳይሆን በውድነህ ክፍሌ ተጽፎ ይቀጥላል::

Kumneger

ቁምነገር መጽሄት ላይ ሞጋቾች ድራማ እና የጀርባ ሙግቱ በሚል ባስነበበው ዘገባው የድራማው ዳይሬክተር መቅደስ ጸጋዬ “ደራሲው ሥራውን ቶሎ ሰርቶ የማጠናቀቅ ችግር አለበት” ስትል መክሰሷን ሲያስነበብ አዲስ አድማስ ጋዜጣ በበኩሉ ለፕሮዲውሰሯ ደውዬ የሰጠችኝ ምላሽ ችግሩ የተፈጠረው ከኔ ጋር ሳይሆን ከሌሎች 3 ሰዎች ጋር ነው የሚል ነው::

የድራማው ደራሲ ኃይሉ ጸጋዬ ከመቅደስ ጋር ስላላግባባቸው ጉዳይ ለአዲስ አድማስ ጋዜጣ ገልጻ ሰጥቷል… እንደወረደ ይኸው:-

በየሳምንቱ ረቡዕ ምሽት በኢቢኤስ ቴሌቭዥን የሚቀርበው የ“ሞጋቾቹ” ተከታታይ ድራማ ደራሲ በሆነው ኃይሉ ፀጋዬና በፕሮዱዩሰሯ መካከል በተፈጠረ አለመግባባት የተለያዩ ሲሆን ድራማው በታዋቂው ፀሐፌ ተውኔት ውድነህ ክፍሌ ይቀጥላል ተብሏል፡፡
የድራማው ደራሲ አንጋፋው የተውኔት ፀሐፊ ኃይሉ ፀጋዬ ለአዲስ አድማስ እንደተናገረው፤ ከዚህ ቀደም በተለያዩ ምክንያቶች ከመቅዲ ፕሮዳክሽን ባለቤትና ዶክተር ኮከብን ሆና በድራማው ላይ ከምትተውነው መቅደስ ፀጋዬ ጋር አለመግባባቶች ይፈጠሩ ነበር፡፡
“አሁን ግን በዋናነት ያጋጨን መቅደስ የታሪኩ አቅጣጫ በሆስፒታሉ ዙሪያ ብቻ እንዲሆን ፈለገች፤ እኔ ደግሞ ሌሎቹም ታሪኮች አስፈላጊ በመሆናቸው በጀመርኩት መቀጠል እንደሚገባኝ ተናገርኩ፡፡ በተጨማሪም የተዋንያን መረጣ (casting) ውስጥ አንተን አይመለከትህም ተባልኩ፡፡ እኔ ደግሞ እስካሁንም ለስራዎቼ ተዋንያን የምመርጠው እራሴ ነኝ፡፡ ሌላው መጠባበቂያ ስራዎች አትስጠኝም ትላለች፤ እኔ ደግሞ ባለው መስራት ይቻላል በቂ ነው እላለሁ፡፡ በነዚህና መሰል ጉዳዮች መግባባት ስላልቻልን በሽማግሌ ተነጋግረን ተለያይተናል፡፡” ብሏል፤ ደራሲ ኃይሉ ፀጋዬ፡፡ ፕሮዲዩሰሯ ከዚህ በኋላ የድራማውን ርዕስና ገፀባህርያቱን መጠቀም ትችል እንደሆነ ጠይቀነው ኃይሉ ሲመልስ፤ ተገቢውንና በቂ ክፍያ ስለፈፀመች መጠቀም እንደምትችል ገልጿል፡፡
መቅደስ ፀጋዬ በበኩሏ፤ “የድራማው ፕሮዱዩሰር እኔ አይደለሁም፤ ሆኜም አላውቅም፤ ሰዎች “መቅዲ ፕሮዳክሽን” ስለሚል እኔ እመስላቸዋለሁ፤ ትልቁ ድርሻ የኔ ቢሆንም ባለቤትነቱ የሦስት ሰዎች ነው፡፡ ፕሮዱዩሰሩ በኃይሉ ነው፤ ለበኃይሉ ደውሉለት” በማለት ከአለመግባባቱ ጋር ለተያያዙ ጥያቄዎች ምላሽ ከመስጠት ተቆጥባለች፡፡

Hailu
መቅደስ እንዲህ ትበል እንጂ ደራሲ ኃይሉ ፀጋዬ ያለ እሷ ሌላ ሰው እንደማያውቅ ነው የተናገረው፡፡ “የትኛውንም አይነት ውል የተዋዋልኩትና ስራዎችን ስሰራ የነበረው ከሷ ጋር ነው፡፡ እኔ እስከማውቀው ድረስ ፕሮዱዩሰሯ እሷ ነች፤ ሽማግሌዎች በመሃል ገብተው ያነጋገሩንም ከሷ ጋር ነው” ብሏል ደራሲው፡፡ መቅደስ የጠቆመችን አቶ በኃይሉ ማሞ በበኩሉ፤ በድራማው ላይ በፕሮዱዩሰርነት የሰራው የመጨረሻዎቹን ሦስት ክፍሎች ብቻ እንደሆነ ይናገራል፡፡ ሆኖም አለመግባባቱ በተከሰተበት ወቅት ሽምግልና ውስጥ ነበርኩበት በማለት ስለሁኔታው ለአዲስ አድማስ አስረድቷል፡፡
“ዋናው የአለመግባባቱ መነሻ የነበረው የስክሪፕት መዘግየት ነው፤ የታሪክና የካስቲንግ ጉዳይ ትልቅ ችግሮች አልነበሩም፤ ዋናው ችግር የስክሪፕት በጊዜ አለመድረስ ነው” ያለው አቶ በኃይሉ፤ አለመግባባቱ የተፈታበት መንገድ ያስደሰተው ይመስላል፡፡ “ሰው አብሮ ከሚሰራው ጋር በብዙ ነገር ይጋጫል፤ ሆኖም ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ በሽምግልና በሰላም ተለያይተናል፡፡” ብሏል፡፡
የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የቲያትር መምህርና አንደኛው አሸማጋይ የነበሩት ረዳት ፕሮፌሰር ሙሉጌታ ጀዋሬ በበኩላቸው፤ “ዋናው ፀብ ፕሮዱዩሰሯ እንዲፅፍ የፈለገችውና እሱ የፈለገው መጣጣም አለመቻሉ ነው፤ በትእዛዝ መፃፍ ደግሞ ይከብዳል፡፡” ብለዋል፡፡
የደራሲ መለወጥ በታሪኩ ላይ የሚያሳድረው ተፅዕኖ አይኖርም ወይ በሚል ተጠይቀውም፤ “በብሎኬት የተጀመረን በጭቃ መጨረስ አይሆንም፤ በጭቃ የተጀመረንም በብሎኬት መጨረሱ እንደዛው ከባድ ነው፤ መሰረቱ ያለው በጀመረው ሰው እጅ ነው፡፡ ይሄ እንዴት ይታረቃል የሚለውን አብረን የምናየው ነው የሚሆነው፡፡ ተመልካች ላይ ተፅእኖ የማሳደሩ ጉዳይ ግን ጥያቄ የለውም” ብለዋል፤ ረዳት ፕሮፌሰር ሙሉጌታ ጀዋሬ፡፡

The post የሞጋቾች ድራማ ደራሲ ኃይሉ ጸጋዬ ከፕሮዲውሰሯ መቅደስ ጸጋዬ ጋር ስላላግባባቸው ጉዳይ ተናገረ appeared first on Zehabesha Amharic.

ህወሀት ”ቅማንት”የሚል አደገኛ ካርድ ስቧል |መሳይ መኮንን

$
0
0

ህወሀት ”ቅማንት” የሚል አደገኛ ካርድ ስቧል። በኢትዮጵያ ምድር ላይ ተፈጽሟል ለማለት የሚከብድ እጅግ ዘግናኝ ድርጊት ተፈጽሟል። የማንነት ጥያቄ ተገቢ ቢሆንም በህወሀቷ ኢትዮጵያ ግን ከጥቅሙ ይልቅ ጉዳቱ የሚያመዝን ነው። የዲሞክራሲ ጥያቄ ባልተመለሰበት ሁኔታ፡ የማንነት ጥያቄ የጨቋኞችን ዕድሜ የሚያራዝም መድሃኒት ነው። ህወሀት ዲሞክራሲን ሊያመጣ ፈጽሞ የሚችል ድርጅት አይደለም። አፈጣጠሩና እወክለዋለሁ የሚለው ህዝብ የአናሳ ቁጥር ያለው በመሆኑ ከዲሞክራሲ መርህ(Majority rule-Minority right) ጋር የሚጻረር ነው።ቢፈለግ እንኳን አይቻለውም።

MelesCisor3

ለዚህም ነው የማንነት ጥያቄን በየቦታው እየቀሰቀሰ ህዝብን ከህዝብ እያናከሰ በስልጣን ላይ መቆየትን የመረጠው። እንዲህ አድርገን ካልገዛን በቀር ስልጣን ላይ መቆየት አንችልም ብለው ሟቹ ጠቅላይ ሚኒስትር በድብቅ የተናገሩት እንዳለ ነገ ከነገ ወዲያ ይጋለጣል። 

እናም ህወሀት ዘንድሮ የሳባት የቅማንት ካርድ መጥፎ አየር ይዛ መጥታለች። በጣም አሰቃቂ በሆነ መልኩ የተገደሉ ኢትዮጵያውያን ቪዲዮ በማህበራዊ መድረኮች ተለቋል። ተመልክቼው ራሴን መቆጣጠር እስኪያቅተኝ ደንግጬአለሁ። ከመነሻው ሂደቱን ስንከታተል ስለነበረ ማን ከዚህ አሰቃቂ ድርጊት ጀርባ እንዳለ በሚገባ ተረድተነዋል። ኢትዮጵያውያን ከምንጊዜውም በላይ ጥንቃቄ ልናደርግ የሚገባን ግዜ ላይ ደርሰናል። ድንበሩን ለማስረከብ በመጪው ወር ቀጥሮ ተይዟል። በጎንደር ዘግናኝ ድርጊት እየተፈጸመ ነው።

እነዚህ ሁለት ክስተቶች በአንድ ወቅት ላይ እንዲሆኑ የተደረገው ያለምክንያት አይደለም። ስለድንበሩ ሌላው የኢትዮጵያ ህዝብ ድምጹን እንዳያሰማ በመንደርና ጎጥ ተከፋፍሎ ሁሉም በየሰፈሩ እርስ በእርሱ እየተጠባበቀ፡ አጥር ሰርቶ፡ እየተደገዳደለ እንዲኖር አድርገውታል። በድንበሩ ጉዳይ ከሱዳንና ከህወሀት ወታደሮች ጋር እየተዋጋ የከረመው ይኧው የጎንደሩ ኢትዮጵያዊ ነው። ይህ ህዝብ ለድንበር ማካለሉ እንቅፋት እንዳይሆን ደግሞ ህወሀት ሌላ ካርድ ስቧል። የቅማንት የማንነት ጥያቄ። ጥያቄው ተገቢ አይደለም እያልኩኝ አይደለም። በህወሀት ተቀናብሮ ይህን ጊዜ ጠብቆ መነሳቱ እንጂ።
ጎንደር ሰሞኑን በተከሰተው ዘግናኝ ድርጊት ተወጥራለች። ለመጪው ሌላ የዕልቂት ዳመና አርግዟል። በመሃል የድንበሩ ማካለል ተፈጻሚ ይሆናል። ምን ይበጃል?

ድንበሩ የጎንደር ብቻ አይደለም። በስለት ተከታትፎ እየተገደለ ያለው ኢትዮጵያዊ ወገናችን ነው። እኔ እዚህ ቪዲዮውን መለጠፍ አልፈለኩትም። በየቦታ ስላለ ማየት የሚቻል ይመስለኛል።

ኢሳት ይህን የህወሀት የዕልቂት ድግስ ለማክሸፍ የሚቻለውን ያደርጋል። እንደ ዜጋ፡ እንደ ኢትዮጵያዊ፡ ከምንም በላይ እንደ አንድ ሰብዓዊ ፍጡር፡ እኔም አቅሜና ሙያዬ በሚሰጠኝ ጉልበትና ዕድል ተጠቅሜ ይህን ኢትዮጵያውያን ላይ የተወረወረውን የጥፋት ሰይፍ ለመመከት ቃል እገባለሁ። ጎበዝ እንደ ትውልድ የምንፈተንበት ዘመን ላይ ነን። መሃሉ ላይ ነን። ወጀብ ከግራና ቀኝ ይዞናል። ተያይዘን ካልወጣን መሃሉ ላይ እንቀራለን። …..ፈጣሪ ኢትዮጵያችንን ይታደጋት!!!!

The post ህወሀት ”ቅማንት” የሚል አደገኛ ካርድ ስቧል | መሳይ መኮንን appeared first on Zehabesha Amharic.


የቅማንት ጉዳይ |ለዚህ ጊዜ ያልሆነ ኢትዮጲያዊነት ኢትዮጲያዊነት አይደለም

$
0
0

ከወንድማገኘሁ አዲስ

ወያኔ በታሪክ ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ ለሀገራችንና ለህዝቧ ከቀመመው መርዝ የቀረውንና የከፋውን በፍጥነትና በትጋት እየረጨ ይገኛል። ከዚህ በከፋ ሁኔታ አደጋ የተጋረጠበት አገር ያለ አይመስለኝም::

(ጎንደር ፋሲል ግምብ - ፎቶ ፋይል)

(ጎንደር ፋሲል ግምብ – ፎቶ ፋይል)

በተለይ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የተቀነባበረው በቅማንት የማንነት ጥያቄ ሽፉን የተለወሰው መሰሪ ተንኮል የቅማንትን ህዝብ አብሮት ለዘመናት በፍቅርና በትስስር ከኖረው የአማራ ህዝብ ጋ ለማፋጀት የተቀመመ እና በእጅጉ የከፋ መርዝ ነው። ይህን ደርጊት እንደ ከዚህ ቀደሞቹ የወያኔ ስውርና ግልፅ ክንውኖች በዝምታ ከተመለከትነው ውጤቱ በአሰከፊነቱ ተወዳዳሪ የሌለው ከመሆኑም በላይ ለጎንደርና ለአማራው ህዝብ ብቻ ሳይሆን ጦሱ ለመላው የኢትዮጲያ ህዝብ እንደሚተርፍ ልንገነዘብ ይገባል።
እነሆ ወያኔ የመጨረሻውን ካርድ መዟል። የሰሜን ምእራብ መሬታችንን ለሱዳን አሳልፎ ለመስጠት የክህደቱን የመጨረሻ ውል ተዋውሎ ለተግባራዊነቱ ደፋ ቀና እያለ ይገኛል። ይህንን ለማድረግ የቀረው እጅግ በጣም አጭር ጊዜ ነው።
ይህንን ድርጊት ካላመከንነው አገራችን ዳግም ዳር ድንበሯ ሊገሰስ፣ ሉአላዊነቷ ሊደፈር ነው። ባካባቢው ያሉ ኢትዮጲያዊያን በሁለት ቢላ ሊታረዱ እጅግ ከተሻለም በባርነት ሲሸማቀቁ ሊኖሩና ቀያቸውን ጥለው ሊሰደዱ ነው። አያት ቅድመ አያቶቻቸው ደማቸውን ዋጅተው አጥንታቸውን ከስክሰው ያቀኑት ፣ ተወልደው የወለዱበት ፣ አድገው ያሳደጉበት፣ ተድረው የዳሩበትን ቀዬ ሊነጠቁ ነው። ከአንድ ወር ገደማ በኋላ የሚያርሱት መሬት፣ የሚጠምዱት በሬ ፣የሚገበያዩበት ገበያ፣ የሚስሙት ቤተስኪያን፣ የሚፀልዩበት መስጅድ አይኖራቸውም።ሩዋንዳ እየተደገመ ነው። የቁጥር ልዩነት ካልሆነ በቀር ሰው እየታረደ ሁሉም ዘግናኝ ድርጊቶች ዘርን መሰረት አድርገው እየተካሄዱ ነው።

ስለዚህ ማንኛውም አገሬንና ወገኔን የሚል ኢትዮጲያዊ ሁሉ
_ ይህንን እኩይ ድርጊት ከወዲሁ ማውገዝ
_ በየአካባቢው ተደራጅቶ የፋሽስቱን መንግስት አገር አጥፊ ተግባራት መመከት
_ በተለይም የጎንደርና የቅማንት ህዝቦች አብሮነታች ሁን ሊያጨልሙ በማንነት ጥያቄ ሽፋን አገራችሁንና ነፍሳችሁን ጭምር ሊነጥቋችሁ ወያኔዎች ደጃፋች ሁ ላይ ናቸውና እምቢታችሁን ዛሬውኑ በማሳዬት
_ በድንበር አካባቢ ያላችሁ ኢትዮጲያዊያንም ምንም አይነት የማካለል ድርጊት እንዳይደረግ በማሰናከልና አንገት ላንገት በመተናነቅ
_ በውጪ የምትገኙ ኢትዮጲያዊያን ለተመድ ፣ ለአለምአቀፉ ማህረሰብ አና ተፅእኖ ሊፈጥሩ ለሚችሉ አገራት እንዲሁም ለታላላቅ የዜና አውታራትበማሳወቅ፣ በከፍተኛ ደረጃ በተደራጀ እና ለየት ባለ መልክ በረሀብና በመቀመጥ በሰላማዊ ሰልፍና በተለያዩ የፈጠራ እንቅስቃሴዎች አለም አቀፍ ትኩ ረትን በመሳብ
_ ኢሳትና ሌሎች የኢትዮጲያውያን የመረጃ ተቋማት ድረገፇች የፓልቶክ ሩሞች ሁኔታውን አሰረመልክቶ ሰፊ ሽፋን በመስጠት፣ ህዝቡን በማስተባበርና በመቀ ስቀስ
_ የፖለቲካ ድርጅቶች ቢያንስ በዚህ ክፉ ቀን ለዚህች መከረኛ አገርና ለዚህ እንግልት ህዝብ ሲባል ልዩነታ ችሁን በይደር አስቀምጣችሁ ሁኔታውን ለመቀልበስ በጋራ በመስራት
_ በትጥቅ ትግል የሚታገሉ ድርጅቶች ከተቻለ ድንበር የማካለሉን እንቅስቃሴ የማወክ ኦፕሬሽን በማድረግ
_ አገር ወዳድ ምሁራን ዲፕሎማቶችና የፖለቲካ ድርጅ መሪዎች ለሱዳን መንግስት ሁኔታው ውሎ አድሮ  የሚያስከትለውን መዘዝ በማስረዳት ከዚህ አጥፍቶ
ሊጠፋ እየተዘጋጀ ካለ ስርአት ጋ ምንም አይነት ውል እንዳይዋዋልና አስቀድሞ የተዋዋለውንም ተግባራዊ እንዳያደርግ አስፈላጊ ሆኖ ከተገኘም አገሪቱ በህዝብ በተመረጠ መንግስት በምትመራበት ወቅት ድርድር ማድረግ ለሁሉም የሚበጅ አማራጭ መሆ ኑን በማስረዳት::
እንዲሁም የተለያዩ ፈጣን የትግል ስልቶችን በማቀነባበርና በማጣመር ተግባራዊ ማድረግ የወቅቱ አገር አድን ተግባር ሊሆን ይገባዋል። ይህንን የወያኔ አገር አፍራሽ ሴራ እያዬንና እየሰማን በዘርና በቡድን ተከፋፍለን የመፍትሄው አካል መሆን ካቃተን የምናጣው የጋራ ቤታችን የሆነችውን አገራችንን ነው።የምናጣው ህዝባችንን ነው። ተጎናፅፈነው የምንዋብበት ባንዲራ እውነትም ጨርቅ የሚሆነው ያኔ ነው። ስለ ኢትዮጲያ የምንቀኘውና የምንዘምረው ሁሉ ውሸት የውሸት ውሸት ነው ማለት ነው። መቼም ሊጠግግ የማይችል የህሊና ቁስል እንደተሸከምን ኖረን ነው የምናልፈው። ለልጆቻችንም የምናወርሳት ኢተዮጲያ አትኖረንም። ለልጆቹ አገር ያላስረከበ አባት ለልጆቿ አገር ያላስረከበች እናት እሱም አባት አይደለም እሷም እናት አይደለችም።
ለዚህ ጊዜ ያልሆነ ኢትዮጲያዊነት ኢትዮጲያዊነት አይደለም::

The post የቅማንት ጉዳይ | ለዚህ ጊዜ ያልሆነ ኢትዮጲያዊነት ኢትዮጲያዊነት አይደለም appeared first on Zehabesha Amharic.

ድምፃዊ ጃሉድ ታሰረ

$
0
0

jah-lude

(ዘ-ሐበሻ) ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በፖሊስ ዓይን ውስጥ ገብቶ ነበር – ይላል ኢትዮፒካሊንክ ዘገባውን ሲጀምር:: በፖሊስ ቢመከር ቢዘከር አልሰማ በሎ በኋላ ላይም ታሰረ ይለናል ዘገባው:: ታስሮ ፍርድ ቤት የጊዜ ቀጠሮ የጠቀበት አርቲስት ጃሉድ ነው:: ለምን ታሰረ? የውስጥ አዋቂ ዘገባውን ይመልከቱ::

The post ድምፃዊ ጃሉድ ታሰረ appeared first on Zehabesha Amharic.

በስደት የሚገኘው የኢትዮጵያ መምህራን ማህበር አስተባባሪ ኮሚቴ የተሰጠ መግለጫ –“ርሃብ የብልሹ ሥርዓት ውጤት ነው!!”

$
0
0

ethiopian teachers

File Photo

File Photo

የሰው ልጅ በተፈጥሮ ያገኛቸውን መሬትን፣ ዕፅዋትን፣ እንስሳትን ፣ ውሃን—–ለጥቅም ያውላቸዋል፤ ይንከባከባቸዋል። እነዚህን የተፈጥሮ ፀጋዎች በወጉ አለመጠቀም ግን ጉዳት ያደርሳል። ኢትዮጵያ በመልክዓ ምድር አቀማመጥና በአየር ንብረት ተስማሚነት የታደለች ነች። ይህን መልካም ገጽታዋን በሳይንስና ቴክኖሎጂ በመታገዝ በእንክብካቤ ይዞ የመጠቀሙ አካሄድ እምብዛም በመሆኑ የተፈጥሮ ሀብቷን የሰውን ኃይል ጭምር በሚያመረቃ ውጤት መጠቀም ስላልተቻለ ችጋር ደባላችን ሆኖ ዘመናት እየተቆጠሩ ነው።ሌላው ቀርቶ አንድ ምዕተ ዓመት በሚጠጋ ጊዜ 40% የነበረው ደን የለበሰ ምድራችን ተራቁቶ አሁን 4% እንኳ መኖሩ ያጠራጥራል። የመሬታችን መራቆትና የዓለም አቀፉም የአየር ንብረት መዛባት ጋር በተያያዘ በየአስር ዓመቱ የሚከሰተው ድርቅ በ100 ሺዎች ለሚቆጠሩ ወገኖቻችን ህልፈት ዋነኛ ምክንያት ሆኗል። በቅርቡ ደግሞ በየአስር ዓመት የሚከሰተው ድርቅ ዑደቱን በየሦስትና አራት ዓመታት እያሳጠረው እንደሆነ ይነገራል።

Read Full Story in PDF

The post በስደት የሚገኘው የኢትዮጵያ መምህራን ማህበር አስተባባሪ ኮሚቴ የተሰጠ መግለጫ – “ርሃብ የብልሹ ሥርዓት ውጤት ነው!!” appeared first on Zehabesha Amharic.

በበርካታ ኢትዮጵያውያን ብርቱ ትግል ቢቢሲ ራድዮ የኦሮሚኛ ቋንቋ ሥርጭት ለመጀመር ፈቃደኛ መሆኑ ተሰማ

$
0
0

(ዘ-ሐበሻ) ቢቢሲ በመካከለኛና በአጭር ሞገድ የትግርኛና የአማርኛ ቋንቋ የራድዮ ስርጭቶችን ወደ ኤትዮጵያና ኤርትራ ለመጀመር እቅዱን ካወጣ በኋላ በርካታ ኢትዮጵያውያን ከአማርኛ እና ከትግርኛ ቋንቋ በተጭማሪ የኦሮሚኛ ፕሮግራምም እንዲጀመር ባደረጉት ሰፊ ትግል የዓለማችን ትልቁ የመረጃ ተቋም የሕዝቡን ጥያቄ መቀበሉን ምንጮች አስታወቁ::
BBC Amharic Oromo Tigrigna

ኢትዮጵያውያን እና የኢትዮጵያ ወዳጆች በዓለም አቀፍ ደረጃ የፊርማ ማሰባሰብ በማህበራዊ ድረገጾች በማድረግ ቢቢሲ የኦሮሚኛ ቋንቋ የራድዮ ስርጭትም እንዲጀምር ግፊት ያደረጉ ሲሆን ተቋሙም በመቶ ሺህ የሚቆጠሩ የሕዝብ ፊርማዎችን ከተመለከተ በኋላ ጥያቄውን ተቀብሏል ተብሏል::

ቢቢሲ በይፋ ይህንን ጥያቄ በቅርቡ ለሕዝብ ያቀርበዋል ያሉት ምንጮች በአማርኛ; በኦሮሚኛ እና በትግርኛ ቋንቋዎች የቢቢሲ ራድዮ ዝግጅቶች በመካከለኛውና በአጭር ሞገድ ለመቅረብ መወሰኑ እንደ ትልቅ ድል ይቆጠራል ብለዋል::

ቢቢሲ የኦሮሚኛ ቋንቋን እንዲጀምር ግፊት ለማድረግ በተደረገው የፊርማ ማሰባሰብ እንቅስቃሴ ውስጥ በአንድነት የተንቀሳቀሱ ኃይሎች በሌሎች ሃገራዊ ጉዳዮች ላይም እንዲሁ በሕብረት ለውጥ የሚያመጡ ጥረቶችን በጋራ እንዲሰሩ ከሕዝብ ጥሪ ቀርቧል::

The post በበርካታ ኢትዮጵያውያን ብርቱ ትግል ቢቢሲ ራድዮ የኦሮሚኛ ቋንቋ ሥርጭት ለመጀመር ፈቃደኛ መሆኑ ተሰማ appeared first on Zehabesha Amharic.

Health |ከባለቤትህ ጋር ስምምነት መፍጠር የምትችልባቸው 7 ዘዴዎች |በተለይ ከሚስቴ ጋር መስማማት አቃተን ለምትሉ ወንዶች

$
0
0

ዕድሜዬ ሰላሳዎቹ መጨረሻ አካባቢ ሲሆን ባለቤቴም በዚሁ ክልል አጋማሽ ላይ ናት፡፡ ለአስር ዓመት ያህል በትዳር ህይወት አሳልፈናል፡፡ ደስ የሚሉ ሁለት ህፃናት ያሉን ሲሆን ሁለታችንም ዲግሪና ቤተሰባችንን ሊያስተዳድር የሚችል በቂ ገቢ እናገኛለን፡፡ ችግሬ ከባለቤቴ ጋር በነገሮች አለመስማማት ነው፡፡ ከሰዎች ጋር ተግባቢና ተጫዋች ስሆን ኧረ ለሌላው ችግርም አማካሪ ነኝ፡፡ ሚስቴ እኔ የማደርገው በብዛት አይጥማትም፣ የሆነ ነገር ገዝቼላት ስመጣ እንኳ አመሰግናለሁ በማለት ፈንታ ማሽሟጠጥና ማጣጣል ነው የሚቀናት፡፡ ይቅርታ የሚባል ነገር ፈፅሞ አልፈጠረባትም፡፡ ስህተቷን በጩኸትና ለቅሶ ለመሸፈን ትሞክራለች፡፡ ቤቴን ለማሻሻል ብዙ ነገሮችን ሞከርኩ፣ ከእኔም ችግር እንዳለ ለመፈተሽ ጣርኩ፡፡ አልሆነም፡፡ በዕውነት እንዳሰብኩት እየሆነም አይደለም፤ ደካከምኩኝ፡፡ ወደ ቤተክርስቲያን እንኳ አብረን እየሄድን ግማሽ መንገድ ሳንጓዝ መጨቃጨቅ እንጀምራለን፡፡ ትዳራችን በሰላምና በፍቅር መዝለቅ ይችል ዘንድ ምን ማድረግ እንደሚገባን ለሌላም ስለሚጠቅም ምክራችሁን ብትለግሱን፡፡

Happy in dreamland

መልስ፡- መቼም ስለትዳር ብዙውን ጊዜ ብናወጋ በቀላሉ የምንጨርሰው አይመስለኝም፡፡ በተለያዩ አምዳችን ላይ አንስተናል፤ በሰዎች ላይም የሚያደርሰውን ተፅዕኖ በመረዳት ብዙ መንፈሳዊና አለማዊ ፀሐፍትም በየፊናቸው አውግተዋል፡፡ አሁንም ቢሆን በየትኛው የትምህርት እርከን ላይ እንደምንመድበው ባይገባንም ትዳር በህይወት ዘመናችን በርካታ ጉዳዮችን የምንማርበት መድረክ እንደሆነ እንረዳለን፡፡ በዕውነት ልክ እንደሌላው ስርዓተ ትምህርት ተቀርፆለት ባለትዳሮች በዘመናቸው የሚማሩበት ዕድል ቢኖር ተመሳሳይ ችግሮች ገነው ባልተፈጠሩ፤ ቢፈጠሩ እንኳ በቀላሉ መፍትሄ ባገኙ ነበር፡፡ በቅድመ ጋብቻ ወቅት የነበረውን ለስላሳ ባህሪና ሁሌ የሚናፈቅ መረዋ ድምፅ በድህረ ጋብቻ ጊዜ ሊጎረብጥና ጆሮ ሊያሳምም ይችላል፡፡

በትዳር ህይወት ውስጥ የሚገኙ ብዙ ነገሮች አሉ፡፡ መቼም የአምላክ በረከቱ የትየለሌ ነው፡፡ ‹መባረክ› በገንዘብና ቁሳዊ ነገር ብቻ መስሎን ከመንገድ ወጣ ማለት ጀመርን እንጂ አሰጣጡ በተለያየ መንገድ ነው፡፡ ላንዳንዶቻችን ብዙዎች እንደምናስበው በንብረት፣ ለሌላኛው በሰው፣ ለሌላው ደግሞ በዕውቀት፣ ለሌሎቻችን በመንፈስ ፍሬዎች (ፍቅር፣ ሰላም፣ ደስታ፣ ትዕግስት፣ ቸርነት፣ በጎነት፣ እምነት፣ የዋህነትና ራስን መግዛት) ይባርከናል፡፡ በእርግጥ ብዙዎች ያለንን አናውቅም፤ ያወቅነውም ቢሆን ያለንን በአግባቡ አልተጠቀምንም፣ ለመጠቀምም ፈቃደኞች ያልሆንን ብዙ አለን፡፡ ያልገባን ነገር ምን መሰላችሁ ያለን የሚበዛልን የያዝነውን በመደበቅና ያለጥቅም ቁጭ እንዲል በማድረግ ሳይሆን እያወጣን ለሌላው እያካፈልን ስራ ላይ ስናውለው ነው፡፡
ሌላው ከፅሑፍህ የምንረዳው ከሰዎች ጋር በጣም ተግባቢ መሆንህን ነው፡፡ ስለዚህ ነገር በእውነት ደስ ብሎናል፡፡ እያንዳንዱ ግለሰብ ሊኖው ከሚገባ ቁልፍ ማህበራዊ ክህሎት ውስጥ አንዱ ከሌሎች ጋር ተግባብቶ መኖር ነው፡፡ አየህ እንደነገርከን ከሰው ጋር መልካም ግንኙነት ሲኖርህ የተለያዩ ሀሳባችን መካፈል ያስችልሃል፡፡ ሰዎችን ከጭንቀታቸው እረፍት እንዲያገኙ ስታደርግ፤ ውስጥህ ያለውን ዕምቅ አቅምና ክህሎት በማውጣት ለሌሎች መፍትሄ መሆን ስትጀምር በእርግጥ ደስ ይላል፡፡ ታዲያ አንተም በዚህ ሂደት ውስጥ ብዙ የምትማራቸው ነገሮች እንዳሉ እውን ነው፡፡ ከሌሎች ሰዎች ትማራለህ፤ ከራስህም ድርጊትና ተሞክሮ እንዲሁም በህይወትህ ከሚገጥሙህ መነሳትና መውደቅ ትማራለህ፡፡ ይህን ወደፊት አጠናክረህ ልትገፋበት የሚገባ መልካም ባህሪና ትልቅ ችሎታም ነው፡፡
አምላክህ እግዚአብሔር በሰጠህም ልጆች በመደሰትህ መልካም ነገር ነው፡፡ በህይወታችን ብዙ የምናማርራቸው ነገሮች እንዳሉን ሁሉ ለቁጥር የሚታክቱ ደስ የሚሉና ስለነዛም ነገር ልናመሰግንባቸው የሚገቡ ስጦታዎች አሉን፡፡ አንዳንዴ ስራ ውለህ ደክመህ፣ ቤትህ ውስጥም ከባለቤትህ ጋር በገጠመህ ጊዜያዊ ችግር ተመስጠህ ሳለህ ልጆችህ በደስታ ሲቦርቁ ስታይ ጭንቀትህን ያስረሱሃል፡፡ ከነበርክበትም ጊዜያዊ ቻናል ያወጡህና ወደ ኤፍ.ኤም… ያስገቡሃል፡፡ ልጆችህን ስታስብ ዛሬንና ነገን የተሻለ ነገር እንድትሰራ ያደርግሃል፤ ያበረቱሃልም፡፡ እንግዲህ ወንድማችን በህይወት ብዙ ተግዳሮቶች ቢኖሩም፣ በቀላሉም አሁን እንደምንላቸው ቶሎ እውን ባይሆኑም መልካም፤ ብሩህና ጥሩ የሆነውን ነገር ባሰብክ ቁጥር መልካምና የተሻለ ነገር ትሰራለህ የሚል እምነት አለን፡፡ መልካም አስብ፣ መልካም ነገር ስራ፣ መልካምም ነገር ይከናወንልሃል፡፡
ወደ ዋናው ቁም ነገሩ ስንመጣ ጥያቄህ ላንተ ብቻ ሳይሆን ለበርካታ ጥንዶችና ባለትዳሮች እንቆቅልሽ የሆነ ነገር ይመስለናል፡፡ በትዳርም ሆነ ማንኛውም ግንኙነት አልጋ በአልጋ የሆነ ምንም ነገር እንደሌለ እናምናለን፡፡ እንዲኖርም የምንጠብቅ ከሆነ የዋህነት ነው፡፡ ነገር ግን በህይወት የሚገጥሙንን ክስተቶች በአግባቡና አዎንታዊ በሆነ መንገድ ለመመለስ ከሞከርን ትዳራችንን ወደ ፈለግነው አቅጣጫ ልናመጣው እንችላለን፡፡ መሰረታዊ ከሆነው የስሜት ፍላጎቶች (የማፍቀርና የመፈቀር፣ ለራስ ያለን መልካም እይታ፣ ራስን የመቻል…ወዘተ) ባሻገር አንዳቸው የሌላኛውን ፍላጎት ማወቃቸው ለትዳራቸው መጠናከርና መሻሻል ወሳኝ የሆኑ ነገሮች ናቸው፡፡
ስለዚህ ጉዳይ በአንድ ወቅት አንዱ ወዳጃችን ሚስቶች ከባሎች ምን ይፈልጋሉ? ባሎችስ ከሚስቶቻቸው ምን ይሻሉ? የሚል ፅሑፍ የላከልንን መነሻ በማድረግና ሌሎችን መፅሐፍት በማጣቀስ የሚከተሉትን ምክሮች ተግባራዊ ብታደርጉ ትዳራችሁን አሁን ካለበት ወደተሻለ ደረጃ ታደርሳላችሁ ብለን እነሆ ብለናል፡፡ አሰጣጣችንም ለአያያዝ ስለሚያመች በአግባቡ በመያዝ በህይወታችሁ እንድትለማመዱ መሞከር የእናንተው ባለጉዳዮቹ ድርሻ ነው፡፡ ለአሁኑ እስቲ ከሚስቶች ፍላጎት እንጀምር፡፡
1. ሁልጊዜ እወድሻለሁ በላት
መቼም ስታገባት ተገደብ እንዳልሆነ ይገባናል፡፡ ወደህና ፈቅደህ ከሆነ ደግሞ ያገባሃት ልብህ ውስጥ ያለውን በማውጣት እወድሻለሁ በላት፡፡ ይህን ማለት እኮ ወጪ የለውም፡፡ ብላት ሌላ ነገር ይሰማት ይሆናል፣ ወይም ይህ ክብሬ ይቀንስብኛል አትበል፡፡ ከአምላክህ ቀጥሎ ክብርህ እርሷ ናት፤ ለርሷም አንተው ነህ፡፡ እዚህ ላይ ታዲያ በል ስላልንህ ብቻ ሳይሆን በእርግጥም ስለምትወዳት ነው ማለት የሚገባህ፡፡ መፅሐፉስ ከተደበቀ ፍቅር ግልፅ ዘለፋ ይሻላል… ሲል አላነበብክምን? አየህ እህቶች ሁሌም ቢሆን መወደዳቸውን በንግግርና በድርጊት እንድታረጋግጥላቸው ይፈልጋሉ፡፡ በእርግጥ የሚከብደው በውስጥህ የሌለውን ፍቅር ለማለት ስትሞክር ነው፡፡ ያ ማታለል ነው፣ በራስ ላይ የከፋ የስነልቦና ችግር መፍጠር ነው፡፡ ገባህ የምንልህ?
2. መረዳትና ይቅር መባልን (Understand and forgiveness)
ከሚስቶችም ሆነ ከሌሎች ሰዎች ጋር ባለን ግንኙነት አንዳችን ሌሎች የሚሉትን ነገር መረዳት መቻላችን ወሳኝ ነገር ነው፡፡ የሚናገሩትንና የሚያደርጉትን ካልተረዳን፣ በነርሱም ቦታ ሆነን ካልተመለከትን አተረጓጎማችንም የተሳሳተ ነው የሚሆነው፡፡ ማንም ሰው ፍፁም ስላልሆነ ባለቤትህም ጥፋት ልትሰራ ትችላለች፡፡ ችግሯን በመረዳት ይቅርታ ለማድረግ ወደኋላ ማለት አይገባህም፡፡ እርሷ እንዳልፈጠረባት ብትነግረንም አንተ ግን ሁሌም ቢሆን ይቅር ከማለትና ከመረዳት መቦዘን የለብህም፡፡ በዚህ ሂደት ውስጥ እርሷን ይቅርታ ማድረግን፣ ትዕግስትን፣ ቻይነትን፣ ታስተምራለህ፡፡
መማር ዩኒቨርሲቲ ገብቶ በመመረቅ ብቻ ነው ለማለት አንደፍርም፣ ይልቁኑ አብረውን ከሚውሉ ሰዎችም መለወጥ እንዳለ እንረዳለን፡፡ ስለዚህ የምንልህ ነገር ከገባህ መልካም ግንኙነት መዝለቅ የሚችለው ይቅር በመባባል ነው፡፡ የምድሩ ብቻ ሳይሆን የሰማዩም የሚቀናው ይቅር ከልብ ስንባባል ነው፡፡ ቂም አርግዞ ብዙ መንገድ መጓዝ አይቻልም፡፡ ጊዜው ሳይደርስ ይጨናገፍና ለችግር ይዳርገናል፡፡
3. በቂ ጊዜ ማግኘትን
ብዙዎች ሆዳችንን ለማሸነፍ አሊያም ዝናን ለማቅረብ ስንል አብዛኛውን ጊዜያችንን በስራ ማሳለፋችን አይቀርም፡፡ መድከማችን ለበጎ ቢሆንም የትዳር ህይወታችንን ግን እንዲጎዳ መፍቀድ የለብንም፡፡ ችግራችን በስራ ደክመን ጀርባችንን ከፍራሽ ላይ ለመጣል ስንጣደፍ የትዳር ህይወታችንንም አብረን እናጋድማለን፡፡ በድካም ያተረፍነውን በሽታ ስንተካከም ወንድማን እህት ሆነን እንከርማለን፡፡ የምንልህ፣ ከገባህ ሚስቶች በቂ የሆነ ጊዜ ከባሎች ማግኘትን ይሻሉና የምትወያይበት፣ አብረኻት የምትዝናናበት፣ ዕቅድህን ነጻና ግልፅ በሆነ መንገድ የምታዋይበት ጊዜ በሚገባ ስጣት፡፡ እግዚአብሔርን ባትፈራ ጥላህ ጊዜ ወደሚሰጣት ቦታ በሄደች ነበር፡፡ ነገር ግን እምነቷ ልቧን እንዳተሸፍት ስለሚከለክላት ስሜቷን ብቻ በማራቅና በመነጫነጭ ዕድሜዋን እንድትገፋ ያደርጋታል፡፡ ስሊሊህ ከዚህ አንጻርም ያላችሁበትን ሁኔታ ማጤን አግባብ ነው እንላለን፡፡
4. ከእምቢታ ይልቅ እሺ መባልን
ብዙውን ጊዜ ባለቤትህም ሆነች ልጃችሁ በሚጠይቁህ ነገር ላይ አይሆንም/እምቢታን ካስለመድካቸው አንተን መሸሻቸው እውን ነው፡፡ ምክንያቱም ሌላም ጊዜ መጠየቅ ቢፈልጉ እንኳ እሺ አይለንም የሚል ግምት ስለሚኖራቸው የጨለመ አመለካከትን ያዳብራሉ፡፡ አሁን ባለው ሁኔታ ሳይሆን በፊት በነበሩ ክስተቶች ላይ ይመረኮዛሉ፡፡ የጠየቁህ አይሆንም ከማለትህ በፊት ደግመህ ለማሰብ ሞክር፡፡ ይህን ስንልህ ሁሉንም ነገር እሺ በላቸው እያልን እንዳልሆነ ይታወቅልን፡፡ በእርግጥም ማለት ከተገባህ ለምን እንዳልካቸውና ለሁላችሁም ጥቅም እንደሆነ ግለፅላቸው፡፡ በተቃራኒው ደግሞ ለምትጠይቀው ነገር አዎንታዊ ምላሽ በመስጠት ግንኙነታችሁን በቀላሉ ሲለወጥ ማየት ትችላለህ፡፡… እሺ ይበልጣል ከሺ… ሲባል አልሰማህም? አየህ ሰዎች እሺ በመባል ከጭንቀት ያርፋሉ፤ የተለያየ መላምቶችን እያሰቡ አዕምሮአቸውን በመጥፎ ነገር ከመሙላት ይተርፋሉ፡፡
5. መደመጥን
ማድመጥ ግንኙነትን ሊያሻሽሉ ከሚችሉ ነገሮች ውስጥ አንዱ እንደሆነ በተለያዩ አምዶቻችን ላይ ያነሳን ይመስለናል፡፡ በንግግራችን ወቅት ሀሳባችንን ሳንከፋፍል ትኩረት ልንሰጥ ይገባል፡፡ ማንኛውም ሰው ሚስቶችንም ጨምሮ ከሚያናግሯቸውና አብረዋቸው ካሉ ግለሰቦች መደመጥን ይሻሉ፡፡ ሚስት ከልቡ እየሰማኝ ነው ብላ የተናገረችውን ቁም ነገር ባለቤቷ እንዳልሰማ ብታውቅ ምንኛ ሊያማትና ባለቤቷ አብሯት እንዳልነበር ስትረዳ እንደሚሰማት መገመት ትችላላችሁ፡፡ ይህ ደግሞ ለርሷ ቦታ እንደማንሰጣት ሊሰማት ይችላል፡፡ በሌላ አነጋገር የምታመጪው ሀሳብ፣ ወሬ የትም የሚገባ አይደለም ነው፡፡ ስለዚህ ጉዳቱ ከማየሉ በፊት በደንብ አድምጣት፣ እየተከታተልካት ለመሆኑም የምልክት ቋንቋ አሳያት፣ ከዛም ባለፈ ያለችውን በትክክል ለመረዳት ደግመህ በሌላ ቋንቋ ንገራት፡፡ ስለዚህ የምንልህ ከጆሮ በዘለለ ባለቤትህን ከልብህ ልታዳምጣት ይገባል ነው፡፡
6. ፍቅርና ርህራሄን
ሌላው ጋብቻን ከሚያጠናክሩትና ውጤታማ ከሚያደርጉ ጉዳዮች መካከል አንዳችን ለሌላኛው የምናሳየው ፍቅርና ርህራሄ ነው፡፡ በንግግራችን ወቅት እባክሽን፣ አመሰግናለሁ ቢቻል ደግሞ ለብቻ የምንጠራባቸው ስም ቢኖረን ጥሩ ነው እንላለን፡፡ ሰዎች በኛ ውስጥ ትልቅ ስፍራ እንዳላቸው የሚገነዘቡት በምንለውና በምናደርገው ላይ በመመርኮዝ ነው፡፡ ችግሩ አንዳንድ ጥንዶች ከተጋቡ በኋላ ይህን ነገር ይዘነጋሉ፡፡ አንዳንዴ ተሳስተው እንኳ ጉንጭ፣ ከንፈር አሊያም ግንባር ላይ ያልተጠበቁ/ድንገተኛ አሳሳም አድርገው አያውቁም፡፡
7. የቤት ውስጥ የልጆች አስተዳደግ ኃላፊነትን መጋራት
ሌላው በጣም ሚስቶች የሚሹትና ባሎች ሊረዷቸው ከሚፈልጓቸው ጉዳዮች ውስጥ አንዱ የቤት ውስጥ ኃላፊነትን መጋራት ላይ ነው፡፡ ሁለታችሁም ሰራተኞች እንደመሆናችሁ ቤት ስትገቡ ይደክማችኋል፡፡ ይህን ከግምት በማስገባት በቤት ውስጥ የስራ ክፍፍል ታደርጋላችሁን? ልጆችንስ በመንከባከብ በኩል ኃላፊነት በሚሰማው መንገድ ትተጋገዛላችሁን? ይህን ካላደረግን ሚስቶች ሊማረሩ፣ ወደፊት ልጅ ሁሉ ሲባል ላይስቡ ይችላሉ፡፡ ሁሉም የጋራ ፍሬዎቻችሁ እንደመሆናቸው በጋራ ልትንከባከቧቸው የግድ ይላል፡፡ እቤት ውስጥ የሚሰሩ ማናቸውንም ነገሮች እርሷ እስክትልህ ድረስ መጠበቅ የለብህም፡፡ ለዚህ ደግሞ ፍትሃዊ የሆነ የስራ ክፍፍልን ማድረግ ይጠይቃል፡፡
እንግዲህ የሰው ልጅ ፍላጎት እንዲሁ በቀላሉ የሚገታ ባይሆንም አቅምህ በፈቀደ መጠን ከላይ የጠቀስናቸውን ምክሮች ተግባራዊ ብታደርግ፣ ጋብቻን የሚያፀናው አምላክም ሲፈርስ ማየት ስለማይሻ ይረዳሃል የሚል እምነት አለን፡፡ ሌላው ልታስታውስ የሚገባው… ባሎች ሚስቶቻቸውን እንደገዛ ስጋቸው መውደድ ይገባቸዋል፡፡ ሚስቱን የሚወድ ራሱን ይወዳል፡፡ የገዛ ስጋውን የሚጠላ ማንም የለም፤ ይመግበዋል፤ ይንከባከበዋል፤ ክርስቶስም ለቤተክርስቲያን ያደረገው ልክ እንደዚሁ ነው… የሚለውን ነው፡፡
ከላይ የዘረዘርናቸውን ነጥቦች ሚስቶችም ተግባራዊ ልታደርጉት ይገባል፡፡ ምክንያቱም ጎጂ የሚፀናው በሁለታችንም ጥረትና በእግዚአብሔር እርዳታ ነው፡፡ ከዚህ በመቀጠል ደግሞ ባሎችስ ከትዳራቸው/ሚስቶቻቸው ምን ይሻሉ? የሚለውን አጠር ባለ አገላለፅ ለማቅረብ እንሞክራለን፡፡
– ባሎች ያላቸውን ችሎታና ክህሎት ሚስቶቻቸው እንዲያምኗቸው ይፈልጋሉ፡፡ ይህን ደግሞ እንዲያውቁት በተለያየ መንገድ ግለፁላቸው፡፡ ላከናወኑትም ተግባር በተለያየ መንገድ አበረታቷቸው፡፡ ጀርባ መታ፣ ሳም፣ ባሌ እኮ ባትሆን… የመሳሰሉትን ነገር ማንሳት ተገቢ ይመስለናል፡፡
– ተጨባጭ የሆነ መረጃ ሳታዩ ባላችሁን አትጠርጥሩ፡፡ በሚያደርጉት ነገር እመኗቸው፤ የሞሳድና የሲ.አይ.ኤ ስራ ከመስራትም ይልቅ ልክ እንደዚህ አይነት ምክር የምታገኙበትን ተቋም መጎብኘት መልካም ነው እንላለን፡፡
– ባሎቻችሁን አንዳንዴ በማይፈልጉት አካሄድ ለመለወጥ አትሞክሩ፡፡ በቀላሉ መለወጥ የምትችሉት መጀመሪያ ራሳችሁን ነው፡፡ ባሎቻችሁ ላይ ስህተታችሁን ለመሸፈን አልቅሶ ማታለልና መቆጣት የሚፈጥረው ዘላቂና የተሻለ ነገር የለም፡፡
– ፍቅር የማይለውጠው ነገር የለምና ፍቅራችሁን ሳትሰስቱ ለግሷቸው፡፡ ያለ እናንተ ማን አላቸው ብላችሁ? ይህንንም በተለያየ መንገድ ማለትም በፅሑፍ፣ በመሳም፣ በማቀፍ፣ የተለያዩ ነገሮችን በመስጠት ግለጡላቸው፡፡
– ባሎች መከበርን ይሻሉና ተገቢው ክብር ስጧቸው፡፡ በሚያመጡት አሳብና ምክር ላይ አሉታዊ አስተያየት ለመስጠት አትቸኩሉ፡፡
ለዛሬ ይህንን ካልን የሚበቃ መሰለን፡፡ ጤና ይስጠን እንጂ ወደፊት በዚህ ርዕስ ላይ በሰፊው እናወጋለን የሚል እምነት አለን፡፡ ከሁሉ በላይ ደግሞ አምላካችሁ በትዳራችሁ ላይ ጣልቃ እንዲገባ ጋበዙት፡፡ እርሱ የሌለበት ነገር በሙሉ ከንቱ ነው፡፡ ቸር እንሰንብት፡፡

The post Health | ከባለቤትህ ጋር ስምምነት መፍጠር የምትችልባቸው 7 ዘዴዎች | በተለይ ከሚስቴ ጋር መስማማት አቃተን ለምትሉ ወንዶች appeared first on Zehabesha Amharic.

Viewing all 8745 articles
Browse latest View live


<script src="https://jsc.adskeeper.com/r/s/rssing.com.1596347.js" async> </script>